Monday, November 11, 2013

የሰው ያለህ


“ ዓይኔን ሰው ራበው 
ዓይኔን ሰው ራበው 
የሰው ያለህ የሰው 
የሰው ያለህ የሰው” 
አለ ያ ታላቁ አርበኛ  ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ 
ባንዳ አገሩን ቢወር ሊያሰማ ኤሎሄ 
ዓይኔን ሰው ራበው አለ እየተጣራ 
በድዮጋን መንፈስ ጮኸ በጠራራ
ጸሐዩዋን ሳያምናት ፋናውን አብርቶ 
ሰው ባይኑ ፈለገ ከገበያው ገብቶ 
እያለ ተጣራ ጮኸ አሰምቶ 
ዓይኔን ሰው ራበው 
ዓይኔን ሰው ራበው 
የሰው ያለህ የሰው 
የሰው ያለህ የሰው 

ከዚያ ካምደ ወርቁ ከአውደ ምሕረቱ  
ከቤተ ልሔሙ ከቅኔ ማኅሌቱ 
በንባብ በቅኔው በመወድስ ዜማው 
በአራራይ፥ በዕዝል፥ በግዕዝ ቅላጼው 
እያለ ተጣራ ጮኸ አሰምቶ 
ማንም ዞር አላለ የለም የሚሰማ  
« ከመ እንስሳ»  ሆኖ የዕለቱ ዜማ 
ዓይኔን ሰው ራበው 
ዓይኔ ሰው ራበው 
የሰው ያለህ የሰው 
የሰው ያለህ የሰው 

ከዙፋን ችሎቱ ከአደባባዩ 
ከሥልጣን ሠገነት ከልፍኝ አስከልካዩ 
አሰምቶ ጮኸ  ዓይኔን ራበው ብሎ 
ያጣውን የሰው ዘር ዓይኑ ተከትሎ 
ከቤተ መንግሥቱም ከተኮለኮሉ 
ሰው አጣ በዓይኑ እንስሳ ነው ሁሉ 
ዓይኔን ሰው ራበው 
ዓይኔን ሰው ራበው 
የሰው ያለህ የሰው 
የሰው ያለህ የሰው 

ገባ ከጉባኤው ከሊቃውንቱ መንደር 
ሰው ሚገኝበትን ጥበብ ሊመረምር 
ምስክር የሆኑት የመጣፉ መምር 
ቢያነጋግራቸው  የመጣበትን ነገር 
ካፋቸው ቢጠብቅ የሰውነትን ሕግ 
ለካስ ችሎታቸው ሰው እንስሳ ማድረግ 
ዓይኔን ሰው ራበው 
ዓይኔን ሰው ራበው 
የሰው ያለህ የስው 
የሰው ያለህ የሰው 

ከሊቀ ኅሩያን ቀሲስ መልአኩ 


1 comment: