Wednesday, November 6, 2013

« ኢየሱስ አለቀሰ» ዮሐንስ 11፥35


ዶክተር ሊሊያን አልፊ (ትርጉም ቀሲስ መልአኩ ባወቀ) 

የሚከተለው መጣጥፍ የግብጽ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ምዕመን የሆኑ ዶክተር ሊሊያን አልፊ « የሰማይ መጽናናት» በሚለው መጽሐፋቸው ካስቀመጡት ጽሑፍ የተቀነጨበ ነው። 

ነዋሪዎቹ በብዙ ሥነ ምግባራቸው በሚታወቁበትና ጌታችን ኢየሱስ ራሱ እረፍት ማድረግ በሚወድበት በቢታንያ በሚገኘው በዚያ ቤት ሕይወት ሰላማዊ ነበር። ነገር ግን ያ ሰላም ብዙም አልዘለቀም። በአልአዛር ሕመም ምክንያት ሐዘን በዚያ ቤት አጠላ። ሁለቱ የአልአዛር እህቶች በፍቅሩና በርህራሄው ከሚያጥለቀልቃቸው ከወዳጃቸው ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ሌላ የሚሄዱበት ሌላ ምንም የላቸውም ነበር። የርሱን እርዳታ ፈልገው ወደጌታችን ላኩ። መልእክቱን ሲልኩ « ጌታ ለጥሪው ምላሽ ሰጥቶ ቶሎ በመምጣት አልአዛርን ይፈውስ ይሆን ወይስ እርሱን በድንጋይ ለመውገር የሚጠባበቁትን የአካባቢውን ሰዎች ለመሸሽ ብሎ ይቀር ይሆን?» ብለው ሳይደነቁ አልቀረም። 

ነገር ግን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በስሜት ወይም በጥንቃቄ ላይ ተመሥርቶ ምንም እርምጃ አልወሰደም፤ ይልቁኑም ጌታ የተራመደው  በሰማያዊው ጥበብ ላይ ተመሥርቶ ነው፤ «  » መክብብ 3፥1 የሞት መልአክ በሩን በኃይል ሲያንኳኳ ፥ጌታ ግን መምጣቱን አዘገየ። ሴቶቹም  ጌታ በሰዓቱ መምጣቱን ለማጣራት ማዶ ማዶ ያዩ ነበር።   

ከጥቂት ጊዜ በኋላ ሞት ወደ እነዚህያ እህቶች ሕይወት ውስጥ ገባ፤ ያነቡት የነበረው የተስፋ በለቅሶ ወደተሸፈነ ምሬትና ውስጣዊ ጩኸት ተለወጠ። ውስጣዊ ማንነቱ በውስጡ እስክናልፍበት ድረስ የማናውቀው ሐዘን በእውነተኛ ቀለሙ ወደእነዚህ እህቶች መጣ፤ 

በወንድማቸው መቃብር ላይ የተቀመጠው ትልቁ ድንጋይ፥ በለቅሶአቸው የማይነቃነቅ፥ በልመናቸው የማይነሳ ነገር ግን በትከሻቸው ላይ መጥቶ የተቀመጠ መስሎ ተሰማቸው። የመጽናናቱ ቃል ሁሉ ከሕመማቸው ሊያሳርፋቸው አንዳች አላደረገላቸውም። ሌላው ቀርቶ፥ በተመሳሳይ ሁኔታ ላይ ለነበሩት ሰዎች፥ ራሳቸው ይናገሩት የነበሩትን  ቃላት አሁን ሰዎች ለእነርሱ ቢደግሙላቸውም ለልባቸው ሊደርስ አልቻለም። 

ነገር ከረፈደ በኋላ ( ብዙዎች ያሰቡት እንደዚህ ነው) ጌታ ደረሰ። ለጌታ ከተናገሩት ንግግር እንደሚታየው ሁለቱ እህትማማቾች ተስፋቸውን ሁሉ አጥተው ነበር። « አንተ በዚህ ሆነህ ኖር ወንድማችን ባልሞተ ነበር» አሉት። ዮሐንስ 11፥22። 

ብዙ ሕዝብ እየተከተለው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ወደ መቃብሩ ወሰዱት፤ በአልአዛር መቃብርም አጠገብ፥ የለቀስተኞቹ እንባና የጌታችንና የመድኃኒታችን እንባ ተቀላቀለ።  እነርሱ ስለ አልአዛር ሞት ያለቅሱ ነበር፤ ኢየሱስ ግን  « ሞት» በሰው « ኃጢአት» በኩል በመግባቱ ያለቅስ ነበር። 

ከጥቂት ደቂቃ በኋላ ግን አዎንታዊ የሆነ አስተሳሰብ ያለው ምእመን እንኳ የማይጠብቀው ነገር ተከሰተ. . .  የሞተው ሰው እየተራመደ ከመቃብሩ ወጣ። የሐዘኑ ጩኸት ወደ ደስታ ጩኸት፥ ለቅሶው ወደ እልልታ ተለወጠ። 

በዘመናት ሁሉ፥ ይህ ተአምር እየተደጋገመ ሲነበብ፥  በሐዘንተኞች ላይ የተስፋ ጥላ ውልብ ሳይልባቸው አይቀርም፦« ያ ተአምር ለምን ለኔ አይሆንልኝም?» የሚል። 

ሁሉን የሚችለውን ልዑል እግዚአብሔር ተእምራት እንዲያሳየን ለመጠየቅ ሙሉ መብቱ አለን። . . . ተአምራት በሕይወታችን እንዲከሰቱም ያለማቋረጥ መጸለይ አለብን። 

ነገር ግን ብዙ ተአምራት የመከሰታቸውን ያህል፥ ተአምራት አግዚአብሔር በልዩ መንገድ የሚሠራባቸው ልዩ ክስትቶች ናቸው እንጂ እግዚአብሔር ቀን በቀን ፍጥረቱን የሚያስተዳድርባቸው የተፈጥሮ ሕጎች አይደሉም። እምነታቸውን በተአምራት ላይ የሚያደርጉ ሰዎች ብዙ ጊዜ ያዝናሉ። እነርሱ ሲጠብቁት የነበረው ተአምር ሳይሆን ሲቀር እግዚአብሔርን ያማርራሉ፥ በእርሱ ላይ ያንጎራጉራሉ፤ አልፎም ተርፎም ይክዱታል። 

እኛ ግን አንድያ ልጁን ስለ እኛ በመስቀል ላይ እንዲሞት አሳልፎ የሰጠንንና  ለእኛ ያለውን ፍቅር ለማሳየት ሌላ ተአምር የማያስፈልገውን አምላካችንን ልንታመነው ይገባል።  « በሕይወት ሆነን ብንኖር ለጌታ እንኖራለንና፥ ብንሞትም ለጌታ እንሞታለን። እንግዲህ በሕይወት ሆነን ብንኖር ወይም ብንሞት የጌታ ነን።» የሚለውን የቅዱስ ጳውሎስን ቃል እንታጠቀው። ሮሜ 14፥8። በመሆኑም ጌታን እንዲህ እንበለው፦ የኔ ውዱ ጌታ በበሽታ ብሆንም፥ ፍትህ በማጣት መከራ ብቀበልም፥ ብሰደድም፥ ብከብርም ሁል ጊዜ የአንተ ነኝ። 

እርሱ በሚያውቀው መንገድ እግዚአብሔር ሦስቱን ወጣቶች ከሚነደው እሳት ለምክንያት ካዳናቸው፥  ብዙዎች ሌሎች ደግሞ በሚነድ እሳት መካከል ሕይወታቸውን ለአምላካቸው እንደሰጡ ማሰብ አለብን። የሰምርኔስ ሊቀ ጳጳስ የነበረው ቅዱስ ፖሊካርፕ በሽምግልና እድሜው  በእሳት ሲቃጠል በተአምራት ሊያድነው እግዚአብሔር ጣልቃ አልገባም። ያ ቅዱስም ያን እሳት አልፈራም። « ሰማንያ ስድስት ዓመት ክርስቶስን ሳገለግለው አንድም ቀን አልተወኝም። አሁን ታድያ ለምንድነው የምክደው? » ነበር ያለው። 

ይልቁኑ፥ መከራው በጸና መጠን ከእግዚአብሔር ጋር የመገናኘት እድላችን ሰፊ ይሆናል። እነዚያ ሦስቱ ወጣቶች ለእግዚአብሔር የቀረቡ ቢሆኑም፥ ከአምላካቸው ጋር ፊት ለፊት የተገናኙት የሚነደው እሳት ውስጥ ነው! እነርሱንም ሆነ ዛሬም በመከራ ውስጥ ያሉት ሌሎችን « በመከራ ውስጥ ባታልፉ ይሻላችሁ ነበር ወይ?» ብላችሁ ብትጠይቋቸው የሚሏችሁ « የሕይወታችንን ዋና ክፍል ልትነጥቁን ትወዳላችሁን? ሕይወት ምንድነው? ሕይወት እኮ ጊዜ ነው። ይህ ጊዜ የእግዚአብሔርን ልጅ በሚነደው እቶን እሳት ውስጥ ያገኘንበት ጊዜ ነው»  ይሏችኋል።    

ስለሆነም በሚነደው የመከራ እሳት ውስጥ እንኳን ብትሆኑ በአምላካችሁ ታመኑ። እንዲህ ብሎ የተናገረውን፦ ተቤዥቼሃለሁና አትፍራ በስምህም ጠርቼሃለሁ፥ አንተ የእኔ ነህ። በውኃ ውስጥ ባለፍህ ጊዜ ከአንተ ጋር እሆናለሁ፥ በወንዞችም ውስጥ ባለፍህ ጊዜ አያሰጥሙህም በእሳትም ውስጥ በሄድህ ጊዜ አትቃጠልም፥ ነበልባሉም አይፈጅህም።እኔ የእስራኤል ቅዱስ አምላክህ እግዚአብሔር መድኃኒትህ ነኝ። ኢሳይያስ 43፥1-3። 


ወደ አልአዛር እንመለስና [ከቤተ ክርስቲያን ታሪክ በትውፊት እንደምንረዳው] ከተአምራታዊ ትንሣኤው በኋላ ለተወሰኑ ዓመታት እንደኖረ፤ በእርሱ ላይ የተከናወነው ተአምራት የጌታን አምላክነት የሚያሳይ ስለሆነ አይሁድ ያሳድዱትና ሊገድሉት ይሞክሩ እንደነበረ እናገኛለን። በመጨረሻም  ለሁለተኛ ጊዜ አርፎ ዓለም ሳይፈጠር ወደ ተዘጋጀለት ዘላለማዊ ቦታ ሄዶአል። በዚያም በሁለተኛው ተአምር ምክንያት የዘገየበትን እውነተኛ እረፍት አግኝቶአል። ለአላዛር ምርጫ ብንሰጠው ኖሮ [ቅዱስ ጳውሎስ እንደመረጠው] እንዲህ ይለን ነበር፦ « የእኔ ፍላጎት እንኳ መሄድ ከጌታዬም ጋር መሆን ነበር ነገር ግን እኅቶቼን ለማጽናናትና የጌታን አምላክነት ለማሳየት በእኔ ላይ የጀመረውን ሥራ ለመፈጸም በሥጋ እንደገና ተመልሻለሁ።» አሜን ። 

No comments:

Post a Comment