Thursday, January 2, 2020

በጨለማው ዓለም የተገለጠው ብርሃን

የጌታን ልደት ከማክበራችን በፊት ያሉት ሦስት ሳምንታት በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ታላቅ ሥፍራ አላቸው። ከዘጠኙ ንዑሳን የጌታ በዓላት መካከል የሚቆጠሩም ናቸው። የመጀመሪያው ሳምንት ስብከት፥ ሁለተኛው ብርሃን፥ ሦስተኛው ደግሞ ኖላዊ ይባላል። በጨለማው ዓለም ብርሃን ሊሆን ወደ ዓለም የመጣውን፥ የእውነተኛውን ብርሃን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ልደት ለመቀበል ልባችንን የምናዘጋጅበት፥ እንዲሁም ነቢያት « ፈኑ ብርሃነከ ወጽድቀከ፤ አቤቱ ብርሃንህንና ጽድቅህን ላክልን» እያሉ መጸለያቸውን የምናስብበት ሁለተኛው ሳምንት ብርሃን ይባላል።
፩. ብርሃን የሕይወት ምንጭ ነው። በዚህ ባለንበት ዓለም ላይ ብርሃን ከሌለ ሕይወት የለም። ሁላችንም እንሞታለን። ለምሳሌ ለፕላኔታችን የብርሃን ምንጭ የሆነችውን ጸሐይን ብንወስድ እንኳ፥ እርሷ ባትኖር ኖሮ፥ ሁላችንም በረዶ ሆነን ነበር የምናልቀው። እጽዋት ሕያዋን የሚሆኑት በብርሃን እንደሆነም ሳይንስ ይነግረናል። በመንፈሳዊ ሕይወትም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሕይወታችን ምንጭ ነው። እርሱ ለእኛ ሕይወቱን ሰጥቶ፥ በሞቱ ሕይወትን አግኝተናል።
፪. ብርሃን የእውነት ምንጭ ነው። ጨለማ የድብቅ ሕይወት ነው። በጨለማ ውስጥ ሁሉ ነገር ሥውር ነው፤ድብቅ ነው። በብርሃን ውስጥ ግን የተሠወረው ሁሉ ይገለጣል። ሁሉም ወደ ግልጥ ይመጣል። እውነተኛው ብርሃን ከመምጣቱ በፊት የጨለማው አበጋዝ ሰልጥኖብን ነበር። የሞት ፍርሃት ነግሦብን ነበር። ነቢዩ ኢሳይያስ በጨለማ እና በሞት ጥላ ለነበሩ ሕዝቦች ብርሃን ወጣላቸው ያለው ለዚህ ነው። እርሱ ብርሃን የሆነ አምላክ ስለመጣልን ዛሬ በብርሃን በእውነት እንመላለሳለን። እውነትም አርነት ያወጣናል።
፫. ብርሃን የደስታ ምንጭ ነው። በምድራችን በዓመት ውስጥ ውሱን ለሆኑ ጊዜያት ብቻ ብርሃን የሚያገኙ አካባቢዎች አሉ። በእነዚህ አካባቢዎች የሚኖሩ ሰዎች በጭንቀት እጅግ ይጠቃሉ። ሳይንቲስቶች ይህን ጭንቀታቸውን ለማቃለል፥ አርቲፊሻል ብርሃን ( ጸይን የሚመስል ለማስቀመጥ ሞክረዋል። ከጭንቀት ነጻ ለመውጣት የጸሐይ ብርሃን ያስፈልጋቸዋል። ነፍሳችን የልብ ደስታ እንድታገኝ፥ የጽድቅ ጸሐይ ኢየሱስ ክርስቶስ በነፍሳችን ላይ ሊያበራ ይገባል።
እርሱ ራሱ እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ ብሎአልናል።