Monday, April 12, 2010

እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ


እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ


ተወዳጅዋ ኦርቶዶክሳዊት ደራሲና ጋዜጠኛ ፥  ፍሬድሪካ ማቲውስ ግሪን በመጽሐፉዋ ላይ ሪቻርድ ኡምብራንድ የተባሉ የሩሜንያ የሃይማኖት መሪ ፥ በኮሚኒስት ሩሜንያ ዘመን አብረዋቸው ታስረው ስለነበሩ ኦርቶዶክሳዊ ካህን የጻፉትን ተርካ ነበር። በዚያን ወቅት የአንድ ገዳም አበምኔት የነበሩት አባ ኢስኩ በኮሚኒስቶች እጅ ብዙ ስቃይና ድብደባ ደርሶባቸው ስለነበር ከስቃዩና ከድብደባው የተነሣ ለሞት ቀርበው ነበር። ከእርሳቸው ራቅ ብሎ ደግሞ አንድ የኮሚኒስት ባለስልጣን የነበረ እንዲሁ ከደረሰበት ድብደባና ግርፊያ የተነሳ ለሞት ያጣጥራል። ሰውየው በሥልጣን ላይ በነበረበት ጊዜ  አባ ኢስኩን  ብዙ ስቃይና ድብደባ ያደረሰባቸው ነው፤ አሁን ግን እርሱም በተራው ከኮሚኒስት ፓርቲው ተወግዶ ለሥቃይና ለግርፋት እስር ቤት የተጣለ ነው።   ነገር ግን ይህ ኮሚኒስት በዚያ ጻእር ላይ እያለ በአጠገቡ ያሉትን ሪቻርድ ኡምብራንድን ደግሞ ደጋግሞ << ይህን የመሰለ አጸያፊ ድርጊት ፈጽሜ (ንስሐ ሳልገባ) መሞት የለብኝም፥>> በማለት እንዲጸልዩለት ይነግራቸዋል።
ራቅ ብለው በታላቅ ሕመም ውስጥ ያሉት ኦርቶዶክሳዊው አበ ምኔት ከተኙበት አልጋ ላይ ሆነው ንግግሩን ይሰማሉ። ከጥቂት ጊዜ በኋላ በአጠገባቸው የሚገኙትን ሌሎች እስረኞች ግራና ቀኝ እንዲደግፉአቸው አድርገው እየተጎተቱ ያ የገረፋቸው ያ ያሰቃያቸውን ለሞት ያደረሳቸው ሰው ዘንድ ደረሱ፤ ከዚያም በአባታዊ ፍቅር ግንባሩን ዳሰሱት፤ እናም ተናገሩት፤
<< ወጣት ነህ፤ ታደርገው የነበረውን አታውቅም ነበር፤ እኔ ይቅር ብዬሃለሁ  ከልቤ እወድሃለሁ፤ እኔ ኃጢአተኛ የምሆን አንተን መውደድ ከቻልኩ፥ ራሱ ፍቅር ሆኖ ሰው  የሆነው ክርስቶስ ምን ያህል እንደሚያፈቅርህ አስብ። አንተ ያሰቃየሃቸው ክርስቲያኖች በሙሉ ፍጹም ይቅርታ አድርገውልሃል፥ ደግሞም ይወዱሃል፥ ክርስቶስ ይወድሃል። አንተ ደህንንነት ለማግኘት ከምትመኘው በላይ፥ ክርስቶስ እንድትድን ይወዳል። አንተ ኃጢአትህ ይቅር ይባል እንደሆነ አስበህ ይሆናል፤ አንተ ኃጢአትህ ይቅር እንዲባል ከምትመኘው በላይ ኃጢአትህን ይቅር ሊል እርሱ ይፈልጋል።አንተ ከእርሱ ጋር በሰማያት ከእርሱ ጋር  ለመሆን ከምትመኘው በላይ ከእርሱ ጋር በሰማያት እንድትሆን ይመኛል፤ እርሱ ፍቅር ነው። አንተ የሚያስፈልግህ ወደ እርሱ መመለስና ንስሐ መግባት ነው።>> አሉት።  ንግግራቸውን  እንደጨረሱ ያ የተኛው የቀድሞ ገራፊ ኮሚኒስት በእንባና በብዙ ስቃይ ሆኖ ኃጢአቱን ሲናዘዝ፥ ገዳማዊው ኦርቶዶክሳዊ አባት ደግሞ የኃጢአት ሥርየትን ያውጁለት ነበር። ሪቻርድ ኡምብራንድ እንደነገሩን፥ ንስሐ የገባው ሰውና ኦርቶዶክሳዊው አባት በዚያው ምሽት አርፈው ወደሰማያዊ አባታቸው ዘንድ ሄደዋል።
ይህን ታሪክ ያነሳንበት ምክንያት እኒያ ኦርቶዶክሳዊ አባት ለዚያ በጸጸት እሳት ለተለበለበው ነፍስ በወቀሳ ቀስት ለተወጋው ሕይወት የሰበኩለት በመስቀል ያሸበረቀ የፍቅርና የተስፋ መልእክት፥ ዛሬም ለእኛ የመድኃኔ ዓለምን ጥንተ ስቅለቱን ለማክበር ለተሰበሰብን ሕያው የሆነ መልእክት ስለሆነ ነው። እግዚአብሔር ይወደናል፤ ከታላቅ ፍቅሩም የተነሣ፥ በእኛ ፈንታ፥ ለኃጢአታችን ሥርየት ይሆን ዘንድ፥ አንድ ልጁን ለሞት አሳልፎ ሰጥቶአል። ይህ ለእርቅ የሆነው ሞቱ ይህ ለድል አድራጊነት የሆነው የመስቀል ጉዞ የብሉይ ኪዳን መስዋዕቶችን በብዙ መንገድ የፈጸመ ስለሆነ ነው ዮሐንስ መጥምቅ << እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ>> በማለት የአዳኙን መምጣት ያወጀው። ዮሐ 1፥29 ። 

Sunday, April 4, 2010

ተነሥቶአል


ፍርሃት የኢየሩሳሌምን ዙሪያ ገባ ከድኖታል። ምንም እንኳ የፋሲካ ሰንበት ማለትም እስራኤላውያን ከባርነት ነጻ የወጡበት መታሰቢያ የሚከበርበት ቢሆንም ከሳምንት በፊት የነበረው ስሜት የለም። ከሳምንት በፊት መሲሁ ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያይቱና በውርጫው ላይ ተቀምጦ ሲገባ፥ ሕዝቡ በሙሉ ሆሳዕና በአርያም እያለ ነበር የተቀበለው፤ አሁን ግን ያ ሁሉ የለም፤ ያ ለህዝቡ የመጣው አዳኝ ተይዞ ተገርፎ ተዘብቶበት ተሰቅሎአል። መሰቀል ብቻ አይደለም ተቀብሮአል፤ ለዚያውም በእንግዶች መቃብር።
ጊዜው ለርሱ ተከታዮች አስቸጋሪ ነበር። ይሁዳ ሸጠው፥ ጴጥሮስ ካደው፥ ማርቆስ  ራቁቱን እስኪቀር ድረስ ልብሱን ጥሎ ሸሸ። ደቀ መዛሙርቱ ሁሉ ትተውት ተበተኑ። ገሚሶቹ ወደ ቀደመ ተግባራቸው ማለትም አሳ ወደ ማጥመዱ፥ ወደ ቀረጡ፥ ገሚሶቹ በፍርሃት ተሸብበው በዝግ ቤት ተቀመጡ።
በሥውር ደቀ መዛሙርት የነበሩት ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ጲላጦስን ለምነው የጌታን መቃብር ገነዙት፥ በአዲስ መቃብር ቀበሩት ፤ አባቶቻችን በትውፊት እንደነገሩን ቅዱስ እግዚአብሔር ቅዱስ ኃያል የማይሞት የማይለወጥ እያሉ ገነዙት፤
የካህናት አለቆች እንደተሳካላቸው ቆጥረው በደስታ ሰከሩ፤ ሥጋውን ለማስጠበቅም በመቃብሩ ላይ ወታደሮችን አቆሙ።
ነገር ግን የፈሪሳውያን ጠንቃቃነት፥ የወታደሮቹ ጀግንነት የዘመናትን ምኞት፥የነቢያትን ትንቢት፥ የሱባዔውን ፍጻሜ ሊገታ አልቻለውም። ማህተመ ድንግልናዋን ሳይለውጥ ከቅድስት ድንግል ማርያም የተለወለደው ጌታ በዚያ በመንፈቀ ሌሊት መግነዝ ፍቱልኝ መቃብር ክፈቱልኝ ሳይል ተነሣ።
ሞት የገዛውና የሞት ምርኮኛ የነበረው  የአዳም የተስፋው ፍጻሜ ከሞት ተነሣ። በክስ ወደ እግዚአብሔር ከሚጮኸው ከአቤል ደም ይልቅ የአዳምን ልጆች ኃጢአት የሚያነጻው ከሞት ተነሣ። አብርሃም በዕፀ ሳቤቅ ተይዞ ያየው በግ የይስሐቅ ቤዛና ምትክ ለአብርሃም ልጆች ቤዛ ሊሆን ከሞት ተነሥቶአል።
ሀ ላንቀላፉት በኩር ሆኖ ተነስቶአል
ከሞት የተነሱ ብዙ ናቸው፤ ወለተ ኢያኢሮስ ከሙታን ተሰታለች። አልአዛር ከሞት ተነሥቶአል። ቀድሞም በብሉይ ኪዳን ብዙዎች ከሞት ተነሥተዋል። የክርስቶስን ሞት ከሌሌቹ የሚለየው በምንድነው ብሎ የሚጠይቅ ቢኖር፥ ምንም እንኳ
ሌሎቹ ከሞት ቢነሡም፥ የተነሡት ሞት በሚገዛው ሥጋቸው ስለሆነ ተመልሰው ሞተዋል። ክርስቶስ የተነሣው ሞት ለገዛን በሙሉ በእንዴት ያለ አኳኋን እንደምንነሳ ምሳሌ ሆኖን ነው የተነሣው። ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች የክርስቶስ ትንሣኤን ትርጉም በተናገረበት አንቀጽ
አሁን ግን ክርስቶስ ላንቀላፉት በኩራት ሆኖ ከሙታን ተነሥቶአል። ሞት በሰው በኩል ስለ መጣ ትንሣኤ ሙታን በሰው በኩል ሆኖአልና። ሁሉ በአዳም እንደሚሞቱ እንዲሁ ሁሉ በክርስቶስ ደግሞ ሕያዋን ይሆናሉና።   15 23 ነገር ግን እያንዳንዱ በራሱ ተራ ይሆናል፤ ክርስቶስ እንደ በኩራት ነው፥ በኋላም በመምጣቱ ለክርስቶስ የሆኑት ናቸው፤
በማለት የክርስቶስ ትንሣኤ ሞትን ድል ያደረገ በአዳም በኩል ወደ ሰው ልጆች የመጣውን የሞት ፍርድ ያስወገደና በኋለኛው ዘመን የሚሆነውን የሙታን ትንሣኤ ያስረገጠ እንደሆነ በመግለጥ ይህ የክርስትናችን ታላቅ ተስፋ እንደሆነ ገልጦአል፤ 1 ቆሮ 15፥21-23።  

ቅዱስ ጴጥሮስም ይህ የክርስቶስ ትንሣኤ የዘመናት ምኞት የተፈጸመበት እንደሆነ ለማመልከት ቅዱስ ዳዊት ከብዙ ዘመን በፊት የተነበየውን ትንቢት በማውሳት የዳዊት ትንቢት የተፈጸመው በክርስቶስ እንደሆነ ይገልጥልናል።  
የእስራኤል ሰዎች ሆይ፥ ይህን ቃል ስሙ፤ ራሳችሁ እንደምታውቁ፥ የናዝሬቱ ኢየሱስ እግዚአብሔር በመካከላችሁ በእርሱ በኩል ባደረገው ተአምራትና በድንቆች በምልክቶችም ከእግዚአብሔር ዘንድ ለእናንተ የተገለጠ ሰው ነበረ፤   እርሱንም በእግዚአብሔር በተወሰነው አሳቡና በቀደመው እውቀቱ ተሰጥቶ በዓመፀኞች እጅ ሰቅላችሁ ገደላችሁት። እግዚአብሔር ግን የሞትን ጣር አጥፍቶ አስነሣው፥ ሞት ይይዘው ዘንድ አልቻለምና።ዳዊት ስለ እርሱ እንዲህ ይላልና። ጌታን ሁልጊዜ በፊቴ አየሁት፥ እንዳልታወክ በቀኜ ነውና።  ስለዚህ ልቤን ደስ አለው፥ ልሳኔም ሐሤት አደረገ፥ ደግሞም ሥጋዬ በተስፋ ያድራል፤ነፍሴን በሲኦል አትተዋትምና፥ ቅዱስህንም መበስበስን ያይ ዘንድ አትሰጠውም። የሕይወትን መንገድ አስታወቅኸኝ፤ ከፊትህ ጋር ደስታን ትሞላብኛለህ።
ወንድሞች ሆይ፥ ስለ አባቶች አለቃ ስለ ዳዊት እንደ ሞተም እንደ ተቀበረም ለእናንተ በግልጥ እናገር ዘንድ ፍቀዱልኝ፤ መቃብሩም እስከ ዛሬ በእኛ ዘንድ ነው። ነቢይ ስለ ሆነ፥ ከወገቡም ፍሬ በዙፋኑ ያስቀምጥ ዘንድ እግዚአብሔር መሐላ እንደ ማለለት ስለ አወቀ፥  ስለ ክርስቶስ ትንሣኤ አስቀድሞ አይቶ፥ ነፍሱ በሲኦል እንዳልቀረች ሥጋውም መበስበስን እንዳላየ ተናገረ። ይህን ኢየሱስን እግዚአብሔር አስነሣው ለዚህም ነገር እኛ ሁላችን ምስክሮች ነን፤ ሐዋ 2፥22-32
ይህ የጴጥሮስ ስብከት በዚህ ዘመን ለምንኖር በሙሉ ታላቅ መልእክት ያለው ነው። ሐዋርያው የሚለን ዳዊት << ሥጋዬ በተስፋ ያድራል>> በማለት በመንፈስ ቅዱስ ተመልቶ የተናገረው፥ የክርስቶስን ትንሣኤ ከሩቅ ተመልክቶ ነው። ክርስቶስ ከሙታን በመነሣቱ ምክንያት ለዘላለም ህይወት ለዘላለም ሕይወት ተስፋ አለኝ አለ።
ይህ የዳዊት ተስፋ የእኛም  ተስፋ ነው። ከንቱ ሆነን የምንቀር አይደለንም። ለኑሮአችን ትንሣኤ አለው። ለሞተው ነገራችን ትንሣኤ አለው። አለቀ አበቃ ደቀቀ ለምንለው ነገር ትንሣኤ አለው። ትንሣኤው በሞትና በመውጊያው በኃጢአት ላይ ድል አድራጊነትን ስላጎናጸፈን ዛሬ እኛም ከጴጥሮስ ጋር፥ እኛም ከዳዊት ጋር ሆነን << ሥጋዬ በተስፋ ያድራል>> እንላለን። ከጳውሎስ ጋር ሆነንም በታላቅ ድምጽ ያገኘነውን ድል እንናገራለን። እንዲህም እያልን፤
ሞት ሆይ፥ መውጊያህ የት አለ? ሲኦል ሆይ፥ ድል መንሣትህ የት አለ?   የሞት መውጊያ ኃጢአት ነው የኃጢአትም ኃይል ሕግ ነው፤   ነገር ግን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ድል መንሣትን ለሚሰጠንለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን።
1 ቆሮ 15 55-57

Saturday, April 3, 2010

በመስቀሉ ሰላምን አደረገ

እግዚአብሔር ሙላቱ ሁሉ በእርሱ እንዲኖር፥ በእርሱም በኩል በመስቀሉ ደም ሰላም አድርጎ በምድር ወይም በሰማያት ያሉትን ሁሉ ለራሱ እንዲያስታርቅ ፈቅዶአልና። ቆላስይስ 1፥19

ምሥራቃውያን ኦርቶዶክሳውያን በሰሙነ ሕማማት የሚገኙት ን ቀናት ታላቁ ሰኞ፥ ታላቁ ማክሰኞ  (Great Monday, Great Tuesday ) እያሉ ይጠሩአቸዋል። በዚያ ልማድ የእኛም ቀዳሚት ሥዑር ታላቂቱ ቅዳሜ በመባል ትታወቃለች። በዚህ እለት አባቶቻችን መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞንን በዜማና በንባብ በመጸለይ፥ በቤተ ክርስቲያንና በክርስቶስ መካከል ያለውን ልዩ የሆነ ፍቅር በማሰብ ክርስቶስ የአዳምን ልጆች ሁሉ ከሲኦል ነጻ እንዳወጣ፥ በአካለ ነፍስ ወደሲኦል ወርዶ በዚያ ላሉት ነጻነትን እንደሰበከ ይናገራሉ፤ ያበሥራሉ፤ የኃጢአት የጥፋት ውሃ እንደጎደለ፥ ዓለም እንደዳነ ለማብሰር ቄጤማ ያድላሉ። ይህም ኖህ ከጥፋት ውሃ በዳነ ጊዜ ርግቡዋን ሲሰዳት ቄጤማ ይዛ መምጣትዋን የሚያመለክት ነው።

Friday, April 2, 2010

የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ

ለመስቀልከ ንሰግድ ኦ ሊቅነ
ወለትንሣኤከ ቅድስት ንሴብህ ኩልነ
ይእዜኒ ወዘልፈኒ

መምህራችን ሆይ ለመስቀልህ እንሰግዳለን
ቅድስት የምትሆን ትንሳኤህንም ሁላችን እናመሰግናለን
ዛሬም ዘወትርም

ዛሬ ቀኑን ሙሉ ስለ እኛ ኃጢአትና በደል የተሰቀለውን አምላክ ስናስብ ነበር። እንዴት የተባረከ ዕለት ነበር። አምላካችን ያደረገልንን አስደናቂ ውለታውን እንድናስተውል አባቶቻችንና እናቶቻችን ይህን ትውፊት ጠብቀው ስላስተላለፉልን ልናመሰግናቸው ይገባል። ክርስቶስ ኢየሱስ በዓይናችን ፊት ተስሎ እንዳይታይ ጠላት ዲያብሎስ አዚም እንዳያደርግብን የአምላካችን ውለታው ተስሎ በዓይናችን ፊት ሊታይ ይገባል። 

Thursday, April 1, 2010

የወደዳቸውን እስከመጨረሻ ወደዳቸው


ዮሐንስ ወንጌላዊ ከሐሙስ ማታ ጀምሮ የተከናወነውን አስደናቂ ክንውን የገለጠው በሚያስደንቅ መንገድ ነው።
ኢየሱስም ከፋሲካ በዓል በፊት፥ ከዚህ ዓለም ወደ አብ የሚሄድበት ሰዓት እንደ ደረሰ አውቆ፥ በዚህ ዓለም ያሉትን ወገኖቹን የወደዳቸውን እስከ መጨረሻ ወደዳቸው። ዮሐ 13፥1

የወደዳቸውን እስከመጨረሻ ወደዳቸው። ምንኛ አስደናቂ አነጋገር ነው። ጌታችን የተቀበለው መከራ ድንገት የሆነ ሳይሆን በፍቅር የሆነ ነው። በሁኔታዎች ላይ ያልተመሠረተ ፍቅር! መለኮታዊ ፍቅር!
ጴጥሮስ እንደሚክደው፥ ይሁዳ እንደሚሸጠው ፥ ደቀመዛሙርቱ እርሱን ጥለው እንደሚሸሹ እያወቀ የወደዳቸውን እስከመጨረሻ ወደዳቸው።

ግሩም በሆነው በጸጋው ዙፋን ፊት በድፍረት እንድንቀርብ ድፍረት የሚሆነን ይህነው። የወደደን ያለምንም ምክንያት ነው። የወደደን ወሰን በሌለው ፍቅር ነው። ኦ ለዚህ ወሰን ለሌለው ፍቅር አንክሮ ይገባዋል።

ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ይህን ፍቅርህን ዕለት ዕለት ግለጥልኝ። ለእኔ ያለህ ፍቅር ወሰን የሌለው ቢሆንም እኔ ግን ውሱን በሆነው የዓለም ፍቅር እየተንገገላታሁ ነኝና።
ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኔ ያሳየኸኝን ድንቅ የሆነውን ትህትናህን እንዳልረሳው አሳስበኝ። ሽርጥ ታጥቀህ የደቀመዛሙርትህን እግር ያጠብከው ይህን ልታስተምረኝ ነውና።
አምላኬ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ህይወቴን በፍቅርህ ሙላው በጸጋህ እጠበኝ።