Saturday, November 9, 2013

ለእኔ ሕይወት ክርስቶስ ሞትም ጥቅም ነው።


የግእዙ ንባብ « አንሰ እመኒ ሐየውኩ ለክርስቶስ። ወእመኒ ሞትኩ ርቡሕ ሊተ፤ እኔስ በሕይወት ብኖር ለክርስቶስ ነው። ብሞትም የሚጠቅመኝ ነው።» ይላል። ግእዙ በሕይወት ብኖር ለክርስቶስ ነው» የሚለውን ግሪኩ « ለእኔ ሕይወት ክርስቶስ ነው» ብሎ ይናገራል።  ግእዙንም ሆነ የግሪኩን ንባብ  (አማርኛው የግሪኩን ተከትሎ ነው የሄደው) በጥንቃቄ ላስተዋለ ሰው  ጳውሎስ ስለ ስለእስራቱና አሁን ስለተጋፈጠው ችግር ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ ስለ ሕይወቱ ያለውን ትርጉም ይገልጣል። 

ጳውሎስ በዚህ ቦታ ላይ በሕይወትና በሞት መካከል ያለውን ትርጕም ይገልጣል። ለጳውሎስ « ሕይወት ክርስቶስ» ነው።» ይህም ማለት መኖር ማለት ለጳውሎስ ከክርስቶስ ጋር መሆን ወይም በክርስቶስ መሆን ነው። ክርስቶስ ሕይወት የሆነበት ኑሮ ምን ይመስላል ስንል በ ቍጥር 22 የፊልጵስዩስ ሰዎችን ጨምሮ ለሌሎች ወይም ለቤተ ክርስቲያን በሙሉ ፍሬያማ የሆነ አገልግሎት መስጠት ነው።   

ሐዋርያው « ለእኔ ሕይወት ክርስቶስ ነው» ካለ በኋላ « ሞት ጥቅም ነው» አለ። ሞት እንዴት ጥቅም ይሆናል ብለን ስንጠይቀው ሞት የሚጎዳኝ የኃጢአት መሣሪያ መሆኑ አብቅቶአል። ይልቁንም ሞት ከክርስቶስ ጋር አንድ የምሆንበትና ለዘላለም ከእርሱ ጋር የምኖርበት መንገድ ነው ይለናል። በቍጥር 23 ላይም « ልሄድ ከክርስቶስም ጋር ልኖር እናፍቃለሁ፥ ከሁሉ ይልቅ እጅግ የሚሻል ነውና»  በማለት እንዲያውም ከሞት በኋላ ያለውን ኑሮ ከሁሉ ይልቅ የተሻለው መንገድ በማለት ይጠራዋል። 

ስለ ሕይወት ያለን እይታ በሕይወት ውስጥ የምናልፍበትን ነገር እንዴት አድርገን መቀበል እንዳለብን የሚወስን ነገር ነው። ሕይወትን የምናየው በምን መልኩ ነው? ወይም በሌላ ቋንቋ ለእኛ ሕይወት ምንድነው?

 መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሕይወት የሚያስተምረን ምንድነው?

ጳውሎስ « ለእኔ ሕይወት ክርስቶስ ነው» በማለት  ከደማስቆ መንገድ ጀምሮ እስከዚያች ቀን ድረስ ክርስቶስ የገለጠለትን እውነት ቁጥብ በሆኑ ቃላት  አጠቃለለው። መጽሐፍ ቅዱስ ስለሕይወት የሚያስተምረን የሚከተለውን ነው። 

1. የሕይወት ምንጭ እግዚአብሔር ነው። 

ልበ አምላክ ዳዊት «የሕይወት ምንጭ ከአንተ ዘንድ ነውና በብርሃንህ ብርሃንን እናያለን።» ይላል።  መዝሙር 35፥9 አስቀድሞ በገነት መካከል የሕይወትን እስትንፋስ እፍ ያለብን ራሱ እግዚአብሔር ራሱ ነው። ዘፍ 2፥7፤ ይህን ሕይወት ሲሰጠን ደግሞ ተመልሰን ወደ አፈር እንድንገባ አልነበረም። እኛን የፈጠረን ሞትን አዘጋጅቶልን አይደለም። ይልቁንም በገነት መካከል  የሕይወትን ዛፍ አዘጋጅቶልን ነበር። ዘፍ 2፥9። ሆኖም ግን ከእርሱ ይልቅ ጠላት ዲያብሎስ ያዘጋጀልንን መረጥን። 

ሕይወትን እንድንመርጥ የእግዚአብሔር አሳቡና ፈቃዱ ነው።
ሙሴ ለእስራኤላውያን በሞአብ ሜዳ « በሕይወትም እንድትኖር፥ አምላክህን እግዚአብሔርን በፍጹም ልብህ በፍጹምም ነፍስህ እንድትወድድ አምላክህ እግዚአብሔር ልብህን የዘርህንም ልብ ይገርዛል።» ብሎአቸው ነበር ዘዳግም 30፥6። 

ሕይወትን መምረጥ የእኛ ድርሻ ነው። 
በዚሁ ክፍል ላይም እንደገና «በፊታችሁ ሕይወትንና ሞትን በረከትንና መርገምን እንዳስቀመጥሁ እኔ ዛሬ ሰማይንና ምድርን በአንተ ላይ አስመሰክራለሁ እንግዲህ አንተና ዘርህ በሕይወት ትኖሩ ዘንድ ሕይወትን ምረጥ»  ዘዳግም 30፥19። 


ሕይወት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። 
ዮሐንስ በወንጌሉ እንደነገረን ያለእርሱ አንዳች የሆነ ነገር የለም። ሕይወት በእርሱ ዘንድ ነች። ማለትም ሕይወት ማለት እርሱ ነው።  የሕይወት ዛፍ እርሱ ነው። (ዘፍጥረት 2፥9፤ ራዕይ 22፥2) የሕይወት መንገድ እርሱ ነው። መዝ 15፥11፤ ዮሐንስ 14፥6)፤ የሕይወት ምንጭ እርሱ ነው። ( መዝ 35፥9) የሕይወት ውኃ እርሱ ነው። ( ዮሐንስ 4፥11፤ ራዕይ 22፥17 ) የሕይወት እንጀራ እርሱ ነው። ( ዮሐንስ 6፥35) የሕይወት ብርሃን እርሱ ነው። ( ዮሐንስ 8፥12) የሕይወት ራስ እርሱ ነው። (ሐዋ 3፥15) የሕይወት ቃል እርሱ ነው። ( ፊል 2፥16) የሕይወት ተስፋ እርሱ ነው። (2 ጢሞቴዎስ 1፥1) የሕይወት ጸጋ እርሱ ነው። (1 ጴጥሮስ 3፥7) የሕይወት አክሊል እርሱ ነው። ( ያዕቆብ 1፥12፤ ራዕ 2፥10) 

No comments:

Post a Comment