Thursday, January 31, 2013

የእስክንድርያ ትምህርት ቤት (ክፍል ሁለት )

Read in PDF
የትምህርት ቤቱ አመሠራረት

የእስክንድርያ ትምህርት ቤት ስንል፥ በዘመናዊ አስተሳሰብ የትምህርት ቤት ሕንፃ አናስብም፤ ሌላው ቀርቶ የቤተ ክርስቲያን ሕንፃ እንኳ አናስብም። ትምህርቱ ይሰጥ የነበረው በአስተማሪው ቤት ነው። (ይህ አሁን በገጠሪቱ ኢትዮጵያ የአብነት ትምህርት ቤቶች እንደሚሰጠው ማለት ነው።) 


ይህ የክርስቲያን ትምህርት ቤት በመጀመሪያ የተጀመረው እንደ ንዑሰ ክርስቲያን (ካታኪዝም) ትምህርት ቤት ነው። ማለትም የክርስትናን እምነት ተምረውና መጽሐፍ ቅዱስን አጥንተው ለጥምቀት የሚዘጋጁ ከአረማዊነት ወደ ክርስትና የገቡ ሰዎች የሚማሩበት ነው። የትምህርት ቤቱ ዲን ንዑሰ ክርስቲያንን ለጥምቀት የሚያዘጋጁ ነበሩ። የትምህርት ቤቱ ዲን የነበረው አርጌንስ በመጻሕፍቱ ውስጥ ስለእነዚህ ንዑሰ ክርስቲያንን አስተማሪዎች (ካታኪስት) ዘግቦአል። አስተማሪው የክርስትናን አስተምህሮና ክርስቲያናዊ ሕይወት ያስተምር ነበር። « ጥምቀትን ለመቀበል ከፈለጋችሁ» ይላል አርጌንስ፥ « በመጀመሪያ የእግዚአብሔርን ቃል መማር አለባችሁ፤ ከቀደመው ከክፋት፥ የአሕዛባዊ ሕይወትና አነዋወር ሥር መለየት አለባችሁ፥ የዋህነትንና ትህትናን መለማመድ አለበኣችሁ። የመንፈስ ቅዱስ ጸጋን ለመቀበል የተገባችሁ የምትሆኑት ከዚህ በኋላ ነው፤»

የስምዖን ዓምዳዊ ጸሎት (ክፍል ስምንት )

Read in PDF

ምዕራፍ ፳፩፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ የሰማያዊው የአብ ልጅ እንድሆን አድርገኝ፤ አማኑኤል ሆይ ከአንተ ጋር አዋሕደኝ። አንተ ከዓለም አስቀድሞ የነበርህ ነህ። . . . 
ምዕራፍ ፳፪፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ በእርሷ እነጻ ዘንድ ቅዱስ ስምህም በልቡናዬ ውስጥ ይታተም ዘንድ፥ አምላካዊት በሆነች እሳት እጠበኝ። ስምህ የሕይወት ውኃ ምንጭ ነውና፤ ስምህ በውስጡ የታተመበት የሕይወት ውኃን ያፈልቃልና፤ 
ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ ለዓለም ሁሉ ሕይወትን የምትሰጥ የሕይወት ኅብስት ነህ። በአንተ በሕይወት እኖር ዘንድ፥ የሕይወትን ኅብስት ስጠኝ። 
ምዕራፍ ፳፫፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ የሰማዩን መንግሥት ፈልጉ ሌላው ሁሉ ይጨመርላችኋል ያልክ፥ አንተ መንግሥትም ሕይወትም ነህ። የሰማዩን መንግሥትና የዘላለምን ሕይወት አገኝ ዘንድ ስጠኝ። 
ምዕራፍ ፳፬፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ አምላካዊት በሆነች እሳትህ አቃጥለኝ፤ ይህችን እሳትበሕሊናዬ ውስጥም አቀጣጥላት፤ ስለእርሷም « እሳትን በምድር ላይ ልጥል መጣኹ፤ እንድትቀጣጠልም እወዳለሁ» ያልህ፤ ክፋትን የሚያበቅሉ እሾሆችን ሁሉ ታቃጥል ዘንድ በኅሊናዬ ውስጥ አንድዳት። 

Saturday, January 19, 2013

የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፤ የእስክንድርያ ትምህርት ቤት

የእስክንድርያ ትምህርት ቤት 
በቀሲስ ቴድሮስ ማላቲ 
ትርጉም በሊቀ ኅሩያን ቀሲስ መልአኩ ባወቀ ተረፈ 

መግለጫ
ከዛሬ ጀምሮ በየሁለት ሳምንቱ የቤተ ክርስቲያንን ታሪክ የሚመለከቱ ጽሑፎችን እናወጣለን። በሚቀጥሉት ተከታታይ ብሎጎች የእስክንድርያ ትምህርት ቤትን በሚመለከት ግብጻዊው ቀሲስ ቴዎድሮስ ማላቲ የጻፉትን ተርጕመን እናወጣለን። አንዳንድ የግርጌ ማስታወሻዎችን እንደየሁኔታው ለማከል እንሞክራለን። 


መግቢያ ስለ እስክንድርያ ቤተ ክርስቲያን 

ክርስትና ወደ እስክንድርያ ከመግባቱ በፊት ቀደም ብሎ፥ ከተማይቱ የዕውቀት መናኸሪያ በሆኑ ብዙ ትምህርት ቤቶቹዋ የምትታወቅ ናት። ከነዚህም ትምህርት ቤቶች መካከል ታላቁ «ሙዚየም» በመባል የሚታወቀውና በፕቶሎሚ የተመሠረተው ነው። ይህ ትምህርት ቤት በምሥራቁ ዓለም እጅግ የታወቀ ትምህርት ቤት ነው። ከ« ሙዚየም» ጋር « ሴራፒየም» እና « ሴባስቲዮን» የተባሉ ትምህርት ቤቶች ነበሩ። እነዚህ ሦስቱ ትምህርት ቤቶች በየራሳቸው ታላላቅ ቤተ መጻሕፍት ነበራቸው። የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊው ጁስቶ ጎንዛሌዝ እንደዘገበው፥ በዓለም የታወቁ ምሑራን ይመሩት የነበረው  የ« ሙዚየም» ቤተ መጻሕፍት፥ በአንድ ወቅት ከሰባት መቶ ሺ በላይ መጻሕፍት ያስተናግድ ነበር። ይህም ማለት በጊዜው እጅግ አስገራሚ የሆነ የዕውቀት ማህደር ነበር። « ሙዚየም» ስሙ እንደሚያመለክተው፥ ለግሪክ እና ሮማውያን አማልክት ለሙሰስ የተበረከተ፥ አያሌ ጸሐፍያን፥ ሳይንቲስቶችና ፈላስፋዎች የተሰባሰቡበትና ምርምራቸውን የሚያከናውኑበት ዩንቨርስቲ ነበር። በእነዚህ ተቋማት ምክንያት እስክንድርያ በዕውቀት ማዕከልነቷ እጅግ ታዋቂ ከተማ ነበረች። በቁጥር የበዙ የአይሁድ ትምህርት ቤቶችም በከተማዋ ውስጥ በየቦታው ነበሩ። 

የእስክንድርያ መልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ በከተማዋ ውስጥ ለሚሰጠው ትምህርት የተለየ ቃና ሰጥቶት ነበር። ይህ እጅግ አስፈላጊ የሆነ ነገር ነው፤ ምክንያቱም ከእስክንድርያ የሚወጣው ምሑራዊ ሥራ፥ የዓለሙን ጥማት የሚያመለክት ነበር።  ምሥጢራዊና የተሸሸገ ጥበብ ያዘለች አገር አ አድርገው በሚመለከቷት በጥንታውያን ግሪኮች ዘንድ ግብጽ እጅግ እጅግ የምትደነቅ አገር ነበረች። ከዚህም በላይ ከምሥራቅ የመነጩት የተለያዩ ትምህርቶችና አስተሳሰቦች ሁሉ ተሰብስበው የተለየ ክምችት ፈጥረው ነበር። ከነቅዱሳት መጻሕፍቶቻቸው የመጡት አይሁድ ብቻ አልነበሩም። ባቢሎናውያን ከነየሥነ ፈለክ ጥናታቸው፥ ፋርሳውያን ከምንታዌ አስተሳሰባቸው መጥተው ነበር። ብዙዎቹም ልዩ ከሆነውና ብዙውን ጊዜ ግራ ከሚያጋባው እምነታቸውና አስተሳሰባቸው መጥተው ነበር። 

በሌላ ቋንቋ ብዙ ባህልና ቋንቋ በአንድነት የሚኖርባት (ኮስሞፖሊታን) የእስክንድርያ፥ከተማ፥ የግብጻውያን፥ የግሪክ፥ የአይሁድ ባህሎች ከምሥራቃውያን የተመስጦአዊ ትምህርት ጋር በአንድነት የሚኖሩባትና ለአዲስ ሥልጣኔ መነሻ ትሆን ዘንድ፥የትምህርት ማዕከል እንድትሆን የተመረጠች የተለየች የዕውቀታዊ ሕይወት ማዕከል ነበረች። ፊሊፕ ሻፍ እንደጠቆመው፥ 
«   እያደገ የመጣ የንግድ፥ የግሪክ እና የአይሁድ ትምህርት ማዕከል እና በጥንታዊው ዓለም ታላቅ የነበረው ቤተ መጻህፍት መቀመጫ የነበረችውና ታላላቆች ከሆኑት የክርስትና ማዕከላት አንዷ የሆነችውና የሮምና የአንጾኪያ ተፎካካሪ የነበች እስክንድርያ፥ የግብጽ መጥሮጶሊስ ነበረች፥ የፍልስጥኤም የሃይማኖት ህይወትና የግሪክ የዕውቀት ይትበሃል አንድ ላይ ሆኖ ፍልስፍናዊ ውይይትና አስተርእዮአዊ እውነቶችን ማስረገጥን ዓላማው ያደረገው የመጀመሪያው የነገረ መለኮት ትምህርት ቤት እንዲከፈት ጥርጊያ መንገድ ከፈተ። 

በዚህ ሁኔታ ውስጥ ቤተ ክርስቲያን እነዚህ ታላላቅ ትምህርት ቤቶች የከፈቱትን የአስተሳሰብ ጦርነት ለመቋቋም፥ የክርስቲያን ተቋም ከማቋቋም ውጪ ሌላ ምንም አማራጭ አልነበራትም። በሐዋርያት ዘመን ምሁራን የሆኑ ክርስቲያኖች በእስክንድርያ እንደነበሩ በእርግጠኝነት መገመት ይቻላል። ለምሳሌ በሐዋ ሥራ 18፥24 ላይ አጵሎስ ስለተባለው ምሑርና መጽሐፍ ቅዱስ አዋቂ የእስክንድርያ አይሁድ ቅዱስ ሉቃስ ሲነግረን እናገኛለን። ምናልባትም አቂላንና ጵርስቅላን ሳይገናኝ በፊት ስለኢየሱስ የተማረው እና የተረዳው በእስክንድርያ ሊሆን ይችላል። 

Friday, January 18, 2013

Statement of Holy Synod Special Meeting, Los Angeles

The Ethiopian Orthodox Tewahido church in Exile put statement concerning the peace and reconciliation of the church. To read Click Here

Friday, January 11, 2013

የስምዖን ዓምዳዊ ጸሎት (ክፍል ሰባት)

Read in PDF

ምዕራፍ ፲፱፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ ፴ ዓመት በተፈጸመ ጊዜ፥ ትጠመቅና ጥምቀትንም ትባርካት ዘንድ መጣህ፤ ዮሐንስ በወንዙ ዳር ቆሞ ሙሽራዪቱን ለማየት ከአዳራሹ የሚወጣውን የንጉሡን ልጅ መምጣት ይጠባበቅ ነበር። እንዲያጠምቅ የላከው እርሱ መንፈስ ቅዱስ ሲወርድና በራሱ ላይ ሲቀመጥ  ያየኸው (የእግዚአብሔር) ልጅ በእውነት እርሱ ነው አለው። አሕዛብ ሁሉ ተስፋ የሚያደርጉት፥ ይህም የቀደመው መንፈሳዊ ልደት ነው። በመገዘር የአብርሃምን ምሥጢር ፈጸመ። ዳግመኛም የሙሴ ምሥጢር ወደ ቤተ መቅደስ በመግባቱ ተፈጸመ። (የቃልን) ምሥጢር ወደዮሐንስ አደረሰው፤ እርሱም የነቢያት ፍጻሜ፥ በመዐልትና በሌሊት መካከል የቆመ፥ አንደኛው እጁ በነቢያት ዕጣ ሌላ እጁ ከሐዋርያት ጋር የሆነ ነው። እርሱ የነቢያት ፍጻሜ፥ የወንጌላውያን ቀደምት ነው። ስለሙሽራው ሲናገር ከእኔ በፊት የነበረ ከእኔ በኋላ ይመጣል ብሎአልናል። የወልድን የፊቱን መልክ ሲመለከት በጣቱ አመለከተ፤ የዓለምን ኃጢአት የሚሸከምና የሚያስወግድ የእግዚአብሔር ልጅ አለ። 

Wednesday, January 9, 2013

በአንዲት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን? (ክፍል አንድ)



የቤተ ክርስቲያን መለያ ባሕርያት 
Read in PDF

በአንቀጸ ሃይማኖታችን ላይ « ወነአምን በአሐቲ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንተ ላዕለ ኵሉ ጉባኤ ዘሐዋርያት፤ ከሁሉ በላይ በምትሆን፥ ሐዋርያት በሰበሰቡዋት በአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን።» በማለት እናውጃለን። ይህ በኒቅያና በቍስጥንጥንያ የተወሰነው አንቀጸ ሃይማኖታችን የቤተ ክርስቲያንን መሠረታዊ ባህርያት ይነግረናል። ምናልባትም የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ያለችበትን ዐቢይ ችግር ለመረዳት የቤተ ክርስቲያንን መሠረታዊ ባህርይ መረዳት ይኖርብን ይሆናል።

በአንቀጸ ሃይማኖታችን መሠረት፤
ሀ. በአንዲት (አሐቲ) ቤተ ክርስቲያን እናምናለን።
ለ. በቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን።
ሐ. በሐዋርያዊት (ጉባኤ ዘሐዋርያት) ቤተ ክርስቲያን እናምናለን።
መ.  ከሁሉ በላይ በምትሆንና በሁሉ ባለች (እንተ ላዕለ ኵሉ) ቤተ ክርስቲያን እናምናለን። 


ሀ በአንዲት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን። 

አንድ ጸሐፊ «የቤተ ክርስቲያን አንድነት ማኅበረ ምእመናን የሚፈጥሩት ሳይሆን ከጌታ የተቀበሉት ነው።» እንዳሉት፥ የቤተ ክርስቲያን አንድነት ምንጩ ቤተ ክርስቲያን በአንዱ በክርስቶስ መመሥረቷ ነው። በኤፌሶን 4፥5-6 ላይ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረን « አንድ ጌታ፥ አንድ ሃይማኖት፥ አንዲት ጥምቀት፥ ከሁሉ በላይ የሚሆን በሁሉ የሚሠራ በሁሉም የሚኖር አንድ አምላክ የሁሉም አባት አለ።» ስለሆነም ቤተ ክርስቲያን በአንዲት ጥምቀት አማካይነት የአንዱ ጌታ አካል የሆነች፥ አንዱን አምላክ የምትቀድስና የምትወድስ፥ በአንዱ መንፈስ የምትመራ ናት። 

Tuesday, January 8, 2013

የቤተ ክርስቲያናችን መሠረታዊ ችግርና መፍትሔው

 በሊቀ ኅሩያን ቀሲስ መልአኩ ባወቀ 


መግቢያ 

በፕሮፌሰር ብራድሊ ናሺፍ  የተጻፈውን ስለጳጳሳት ሐዋርያዊ ተልእኮ የሚያትተውን ጽሑፍ በጡመራ መድረካችን ላይ ካስቀመጥንበት ጊዜ ጀምሮ የተለያዩ አስተያየቶች ደርሰውናል። በዋናነት የሚጠቀሰው ግን ምንም እንኳ ፕሮፌሰር ናሺፍ ያነሡዋቸው ነጥቦች በወል ሁሉንም አብያተ ክርስቲያናት የሚዳስሱ ቢሆኑም፥ የእኛን ቤተ ክርስቲያን ዐበይት ችግሮች በጥልቀት የሚዳስሱ ጽሑፎች ስለማስፈለጋቸው ነው ምንምን እንኳ ይህ የሁላችንንም ተሳትፎ የሚጠይቅ ቢሆንም እኛ ቃል እንደገባነው በፕሮፌሰሩ መነሻ ነጥቦች ላይ በመመርኮዝ ቤተ ክርስቲያናችን አሁን ባለችበት ሁኔታ ላይ የሚያጠነጥነውን ጽሑፍ የመጀመሪያ ክፍል አቅርበናል።
ወደጽሑፋችን ዋና ሐሳብ ከመግባታችን በፊት ግን የሚከተሉትን ነጥቦች ለማስጨበጥ እንሞክራለን። አንደኛ ቤተ ክርስቲያናችን አሁን ላለችበት ሁኔታ ተጠያቂ የምናደርገው አንድን ቡድን ወይም አካል ሳይሆን ሁላችንንም ነው። ይህን የምናደርገው ለይምሰል ወይም የዘመናዊ ሐሳብ ፍሰት አካሄድ ስለሆነ ሳይሆን፥ እነ ዳንኤል እነ ኤርምያስ ስለሕዝባቸው ስለአገራቸው ያላቸውን ጭንቀት በገለጡበት ወቅት የተከተሉትን መንፈስ ተከትለን ነው።

ሁለተኛ ይህን ለቤተ ክርስቲያናችን ይጠቅመናል የምንለውን ሐሳብ የምናቀርበው ለቤተ ክርስቲያኒቱ እውነተኛ ልጆች ነው። እውነተኛ ልጆቹዋ እነማን እንደሆኑ የሚያውቀው እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ሲሆን ውጫዊ ምልክቶች ግን አሉዋቸው። ከእነዚህም ምልክቶች ዋነኛው ፍቅር ነው። አገልግሎት የሚመነጨው ከዚህ ፍቅር ነው። እምነታቸው እንኳ ለገላትያ ሰዎች ቅዱስ ጳውሎስ እንደጻፈው « በፍቅር የሚሠራ እምነት» ከዚህ የተነሣ እውነተኛ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች ስለሚጠፉት ሰዎች ይገዳቸዋል። በእንባና በጸሎት ያስተምራሉ ይመክራሉ የመድኃኔ ዓለምን ሞቱንና ትንሣኤውን ይመሠክራሉ።

Monday, January 7, 2013

About Professor Nassif's Article

The link for the original article on The Apostolic mission of Bishops by Professor Bradley Nassif is http://www.antiochian.org/node/20229 . As you can see in my translation I tried to contextualize opening paragraph of the article with out altering the original meaning.  I don't want to introduce the recent conflict in Antioch or OCA or Greek Orthodox Churches to the readers. We have more than enough. 

Sunday, January 6, 2013

የስምዖን ዓምዳዊ ጸሎት (ክፍል ስድስት )

ምዕራፍ ፲፯፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ ከእንቅፋት ደንጋይና ከኑፋቄ ጦር አድነኝ። የክብርህን ውበት ይመለከቱ ዘንድ አእምሮዬንና ልቡናዬን አንድ አድርግልኝ። ዳግመኛም ከውድቀት ቅድስት በምትሆን ትንሣኤህ አድነኝ። አንተ የሕይወት ትንሣኤ ነህና። ያንተን አምላክነት የሚጠራጠር፥ በዘላለም ውድቀት ውስጥ ይወድቃልናል። በአንተ በአምላክነትህ የሚታመን ደግሞ ሕይወት በተመላች፥ ሞትና ውድቀት በሌላት ትንሣኤ በክብርህ ይነሣል።ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ ቅድስት በምትሆን ትንሣኤህ አስነሣኝ። እንወደድከው እንደፈቃድህም መግበኝ።

ምዕራፍ ፲፰፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ ሥጋዊ በሚሆን አካል (በየጥቂቱ) ያደግህ፥ ለአንተ ቅድስተ ቅዱሳን እሆን  ዘንድ፥አምላካዊት የሆነች አእምሮ ትጨምርልኝ ዘንድ፥ መንፈሳዊት በሆነች መታነጽ ታንጸኝና ታሳድገኝ ዘንድ እለምንሃለሁ።  

Friday, January 4, 2013

Review on Les Misrable

If you want a review of Les Mis from Christian perspective you can read Christianity Today. I know it is Evangelical magazine, but I like its cultural and ecumenical commentary. I read Les Miserables when I was young and its powerful story is the story of redemption and forgiveness and it is the story of Christianity.  

Thursday, January 3, 2013

የኦርቶዶክሳውያን ጳጳሳት ሐዋርያዊ ተልዕኮ፤ አጭር አስተያየት።


በዶ/ር ብራድሊ ናሲፍ 
ትርጉም በሊቀ ኅሩያን ቀሲስ መልአኩ 

መግለጫ
ጸሐፊው ዶክተር ብራድሊ ናሲፍ የአንጾኪያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አባል ሲሆኑ በቺካጎ ኖርዝ ፓርክ ዩንቨርስቲ የነገረ መለኮት ፕሮፌሰር ናቸው። ጽሑፋቸው በዚህ ዘመን በኦርቶዶክሱ አለም ለሚታየው ከፍተኛ ቀውስ ቆም ብለን የምናስብበት ታላቅ ትምህርት የሚሰጥ ነው። እዚህ ላይ የተረጎምነውም ለኛዋ ቤተ ክርስቲያንም ታላቅ ትምህርት ይሰጣል ብለን በማሰብ ነው። መልካም ንባብ።

የዚህ አጭርና ያልተሟላ አስተያየት ዓላማ፥ በኦርቶዶክሳዊ ሊቀ ጳጳስ የወንጌል አገልግሎት ማዕከላዊነት ላይ ትኩረት ለመስጠት ነው። ይህ ጽሑፍ በጊዜያችን በኦርቶዶክሳውያን አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ ያለውን ችግር አንዱን ወገን ወግኖ ለማየት አይደለም። ዓለማው ሊቀ ጳጳሱ የተጠራለትን ሕይወት ለማሳየት ነው። በየትኛውም ሥፍራ ይሁን በማናቸውም ሁኔታ ውስጥ፥ የሊቀ ጳጳሱ ተቀዳሚ ሥራ ሊሆን የሚገባውን ለማሳየት በአዎንታዊነት የቀረበ አስተያየት ነው። በእኛ መካከል ሊቀ ጳጳሱ በሚሰጠው አገልግሎት ውስጥ የክርስቶስ ወንጌል ማዕከላዊ እንደሆነ መረዳት እጅግ አስፈላጊ ነገር ነው። 

በኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሊቀ ጳጳሱ ሐዋርያዊ ተልዕኮ በአምስት ነጥቦች ሊጠቃለል ይችላል።  

  1. ወንጌልን መስበክ። 
ኦርቶዶክሳውያን ጳጳሳት የክርስቶስን ወንጌል ለቤተ ክርስቲያንና ለዓለም ማወጅና መተርጐም አለባቸው። ጳጳሳት ሊመረጡ የሚገባቸው በይበልጥ ቅዱሳት መጻሕፍትን በማወቃቸውና ለሌላው ለማስረዳት ባላቸው ችሎታ መሆን አለበት። ለእንዲህ ዓይነቱ ጳጳስ በምሳሌነት ሊጠቀስ የሚችለው ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ነው። ኦርቶዶክሳውያን ጳጳሳት ወንጌልን በታማኝነት ሊከተሉና የአገልግሎታቸው ማዕከል ሊያደርጉ ይገባል። 

Wednesday, January 2, 2013

የስምዖን ዓምዳዊ ጸሎት ክፍል አምስት

READ In PDF

ምዕራፍ ፲፬፡ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ በኃጢአት የሞተችውን ነፍሴን ፈውሳት፤ ስምህን ለማመስገንም አንቃት።
ምዕራፍ ፲፭፡ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ አርባኛው ቀን በተፈጸመ ወት አንተ የቅዱሳን ቅዱስ ስትሆን፥ ቁርባናትን ያመጡ ዘንድ ሙሴን ያዘዝከው አንተ ስትሆን፥ በእጁ የሰጠኸውን ሕግ ትፈጽም ዘንድ አርባኛው ቀን በተፈጸመ ወቅት ወደ ቤተ መቅደስ የመጣህ፥  ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ ልቤ መቅደስህ ይሆን ዘንድ አድርገው፥ ሕሊናዬም በፊትህ ተቀባይነት ያለው ቁርባን እንዲሆን አድርገው። አንተ ተቀባይነት ያለው ቍርባን፥ ከአባትህና ከመንፈስ ቅዱስም ጋር ቍርባንን የምትቀበል ነህና።
ምዕራፍ ፲፮፡ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ ስምዖን በክንዱ የተሸከመህና ወደ ቤተ መቅደስ ያስገባህ፥ልቤና ሕሊናዬ   ወደ ቅድስተ ቅዱሳን ይሸከሙህ፥ በዚያም ታላቁን ብርሃንህን ይመልከቱ።ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ ከዚህ ኃላፊ ከሆነው ዓለም እስራት ነጻ እንድታወጣው ስምዖን እንደለመነህ፥ ልመናውንም እንደፈጸምክለት፥ የእኔንም ልመና ፈጽምልኝ፤ ከዚህ ከንቱ ከሆነው ዓለም እስራትም ፍታኝ።ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ ስምዖንን ከዚህ አለም ፍላጎት ነፃ እንዳደረግኸው፥ እንዲሁ የእኔንም ልቡናና ሕሊናዬን ከዚህ ፈራሽ ከሆነው ዓለም ቀንበር ፍታው።