Sunday, November 10, 2013

አንዳንድ ነጥቦች ስለ ሶርያ ክርስቲያኖች

በሶርያ በመካሄድ ባለው የእርስ በእርስ ጦርነት ላይ ሕልውናቸውን የማጣት አደጋ ውስጥ የገቡት የአገሪቱ ቀደምት ነዋሪዎች የሆኑትና ከሁለት ሺ ዓመታት በላይ ሶርያን ቤታቸው አድርገው የኖሩት የሶርያ ክርስቲያኖች ናቸው። ብዙዎች ተንታኞች እንደሚናገሩት በዚህ በጦርነቱ ክርስቲያኖች በሁለት በኩል አጣብቂኝ ውስጥ ወድቀዋል።

በአንድ በኩል እነርሱን ከምድረ ገጽ ለማጥፋት ቆርጠው የተነሱ እስላማውያን « ነጻ አድራጊዎች» ተደርገው በምእራባውያን ሁሉ ሲደገፉ፥ በሌላ በኩል ደግሞ በምዕራባውያኑ ዘንድ አምባ ገነን ተብሎ የሚታወቀው የአሳድ አገዛዝ ከሚከተለው ዓለማዊ ( secular) አስተዳደር አንጻር ለክርስቲያኖች ውሱን የሆነ ነጻነት ሰጥቶአቸዋል።
« የሚያውቁት ሰይጣን፤ የሶርያ ክርስቲያኖች ለምን ባሽር አልአሳድን ይደግፋሉ » በሚል ግሩም መጣጥፉ ላይ  ገብርኤል ሰኢድ ራይኖልድ የተባለ ጸሐፊ፥ ገና በጦርነት ላይ ያሉት እስላማውያን ተዋጊዎች በያዙዋቸው አንዳንድ ከተማዎች ላይ በክርስቲያኖች ላይ ያደረሱትን በደል በዝርዝር ገልጦአል።

አብያተ ክርስቲያናትን ከመመዝበር አልፎ ተርፎ፥ ካህናቱን በገጀራ እስከማረድ ድረስ ዛሬ በሶርያ የሚታይ ድርጊት በመሆኑ፥ በዚያ ያሉት ክርስቲያኖች ምንም እንኳ ባሽር አልአሳድ የሚያኮራ የሰብአዊ መብት ሪኮርድ የሌለው ቢሆንም ከእርሱ ጋር መወገንን መርጠዋል።

ከሁሉ የሚያሳዝነው የምዕራባውያን መንግሥታት ነው። እንኳን በሶርያ ላሉት ክርስቲያኖች ቀርቶ፥ በቍጥር በዛ ያሉና በምዕራባውያን መንግሥታትም ዘንድ ተሰሚነት ይኖራቸዋል የሚባሉት የግብጽ ክርስቲያኖች በእስላማውያኑ እየደረሰባቸው ያለውን መከራና ስቃይ እንዴት በዝምታ እንዳለፉት ዓለም የሚያውቀው ነው።

ዛሬ ስለ ኢራቅ ክርስቲያኖች የሚያወራ ማን ነው። ነገር ግን የኢራቅ ክርስቲያኖች ላለፉት ሁለት ሺ ዓመታት በኢራቅ ውስጥ የኖሩ ከኢራቅ ቀደምት ነዋሪዎች መካከል የነበሩ ናቸው። ከሳዳም መውደቅ በኋላ ግን እስላማውያኑ የኢራቅ ክርስቲያኖችን ከኢራቅ እንዲጠፉ ነበር ያደረጉአቸው። ይህ አይነቱ ድርጊት በእነርሱ የሚደገም ስለመሰላቸው የሦርያ ክርስቲያኖች ስደትን በመምረጥ ፓስፖርታቸውን እያዘጋጁ መሆናቸውን ብሉምበርግ የተባለው የዜና ማሰራጫ ገልጦአል።

በጎረቤት አገር በኬንያ ስላለው እስላማዊ እንቅስቃሴና በእኛም አገር ቢሆን በዲያስፖራውም ሆነ በሥልጣን ላይ ባለው መንግሥት ያለውን እይታ በሰፊው መጣበታለሁ። 

1 comment:

  1. please kesis በዚህ ጉዳይ በሰፊውና በቶሎ እንድትጽፈው በተለይ ለሃገር ቤት ላለነው ጉዳዩ አንገብጋቢ ነው!

    ReplyDelete