Thursday, June 20, 2013

ራስ ከራስ ( ማሰላሰል)


ነፍሴ ሆይ በገናናው ዙፋኑ ፊት ራስሽን አዋርጂ፥ የታረደልሽ ጌታ ሕያውና በክብር ያረገ ነውና፤ በዚህ ዓለም ኹከትና ብጥብጥ ላይ ታች አትበይ፤ ኃጢአትሽን የተሸከመልሽ የቀራንዮው በግ በሰማይም በምድርም ጌታና አዳኝ ነውና ተስፋሽን በእርሱ ላይ አድርጊ፤ ታላቁ አባት ስምዖን አምዳዊ ይህን ጌታ እንዳመሰገነው አመስግኚው፥ አግንኚው አምልኪው፤

ነፍሴ ሆይ ውለታውን ተናግረሽ አልጨረሽም፤ እንኳን ውለታውን ተናግረሽ ለመጨረስ፥ የተደረገልሽን ገና ሙሉ በሙሉ አላስተዋልሽም፤ ገና በድንግዝግዝ ነሽ፤ ከዕውቀት ገና ከፍለሽ ነው ያወቅሽው፤ በዕውቀቱ እስክትሞይ ድረስ ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ እስክትደርሺ፤ የጸጋው ሙላት እስክትዋኚ አክብሪው፥ አንግሽው፤

ነፍሴ ሆይ በዚህ ሰዓት በመላው ዓለም በብዙ ችግር ውስጥ ሆነው ለአምላካቸው ስም በጽንዓት የቆሙትን አስቢያቸው፤ በሦርያ ያሉትን ክርስቲያኖች፥ በኢራቅ ያሉትን ክርስቲያኖች፥ በግብጽ ያሉትን ክርስቲያኖች፥ መኖራቸው እንኳ ምስክር የሆነውን በሞታቸው ዋጋ የሚከፍሉትን አስቢያቸው፤ እናም ነፍሴ ሆይ ለአምላክሽ ዛሬ እንዴት ሆነሽ ዋልሽ፡ . . . .

No comments:

Post a Comment