Thursday, June 20, 2013

ግላዊ ሕይወት፥ ግላዊ ነጻነትና እና የአዲሱ ዘመን ተግዳድሮት፤ ለውይይት መነሻ አሳብ

ከሰሞኑ አፈትልኮ የወጣው ምሥጢራዊ ሰነድ እንዳመለከተው ከሆነ፥ በዚህ በአገረ አሜሪካ የሚገኘው የብሔራዊ ጸጥታ ድርጅት (National Security Agency) የዜጎችን የዕለት ከዕለት እንቅስቃሴ በተለይም በኤሌክትሮኒክስ መልክ የሚካሄደውን የመረጃ ልውውጥ እንደሚከታተል ወይም እንደሚሰልል ነው። ይህ ስለ አገር ጸጥታ በሚያስቡ ወገኖች ዘንድ ትልቅ ራስ ምታት ሲሆን በአንጻሩ ደግሞ የግለሰብን ነፃነትና መብት ለማስከበር ደፋ ቀና ከሚሉት ጀምሮ ስለ ሃይማኖት ነፃነት እስከሚያስቡ ድረስ፥ በግለሰቦች ሕይወት ውስጥ የመንግሥት ሚና ምን ያህል መሆን አለበት የሚል ከፍተኛ ክርክር አስነስቶአል። አንዳንዶች አሁን ካለው ዓለም አቀፋዊ ከሆነው የሽብርተኝነት እንቅስቃሴ አንጻር መንግሥት ምንም አማራጭ እንደሌለው ሲናገሩ፥ ሌሎች ደግሞ ይህ አይነቱ እጅግ የተንሰራፋ ሥልጣን ፍጻሜው ምን ይሆናል ይላሉ።

ቤተ ክርስቲያን በዚህ ዓይነቱ ውይይት ላይ ድምጽ ሊኖራት እንደሚገባ እሙን ነው። ለምሳሌ ሃይማኖታዊ ነጻነትን የሚጋፋ ነው ወይ? በአበ ነፍስና በተነሳሒው መካከል የሚኖረውን ምሥጢራዊ ግንኙነት የሚደፍር ነው ወይ? በአሁኑ ወቅት ካለው የጥድፊያ ኑሮ አንጻር አንዳንድ ጊዜ የምክር አገልግሎት በኤሌክትሮኒክስ የመረጃ ልውውጥ ሲከናወን ይታያልና።

ያም ሆነ ይህ በአገርና በሕዝብ ላይ ጉዳት የሚያመጡትን አሸባሪዎች ለመያዝ  የሚደረገው ጥረት ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ሁሉ የግለሰቦች መብት በምን መንገድ መከበር እንዳለበት ሰፊ ውይይት ሊደረግ ይገባል ለማንኛም ግን እጅግ በማደንቀው በቴክኖሎጂ መዝናኛ እና ንድፍ ባለሙያዎች ስብሰባ ላይ ታዋቂው የቴክኖሎጂ አታቲJuan Enriquez  ያስቀመጠውን ንግግር በማስተዋል ማድመጥ ይገባል፤

ዩአን የሚለን ነገር ቢኖር፥ በድረገጽም ሆነ በሌላም የዲጂታል መገናኛ ዘዴዎች የምንለዋወጣቸው ነገሮች የእኛን ዘመን አልፈው የሚኖሩ ናቸው፤ ጥያቄው ያን እያሰብን ነው ወይ የምንነጋገረው፤ ብዙዎቻችን ዛሬ ማንም አያየውም ያልነው ግላዊ ነጻነቶች (private activities) ነገ የአደባባይ ምሥጢሮች ናቸው። ነገ ስንል ከሞትን በኋላ አይደለም። ቃል በቃል ነገ። ተወያዩበት። 

No comments:

Post a Comment