Monday, June 24, 2013

ጸሎተ ስምዖን ዓምዳዊ (ክፍል 12)

ምዕራፍ ፴፮፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ፥ ወደ ቃና ዘገሊላ ሠርግ የተጠራህ፤ ውኃውን ለውጠህ መልካም መዓዛ ያለው የሚያረካ ወይን ያደርግኸው፤ ኅቡእ የሆነው እይታህ፥ ወደእነዚያ የድንጋይ ጋኖች የወረደ፤ የውኃውን ጠባይ የቀየረ፥ ጣዕሙ መልካም የሆነ ወይን ያደረገው ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ፥ ያ ኅቡእ የሆነው እይታህ ወደ ሕሊናዬ ውስጥ ይውረድ፤ ከንቱ ከሆነውና ከሚጠፋው ከዚህ ዓለም አሳብ ወደ አዲሱ ዓለም አሳብ ይለውጠው። ከእኔም ላይ አሮጌውን ሰው ይግፈፈው አዲሱን ሰው ያልብሰኝ።

ምዕራፍ ፴፯፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ አዲስ ምርጥ ዕቃ እንድሆን አድርገኝ፥ አዲሱንም ወይን በውስጤ ጨምር በምሕረትህም አድሰኝ።

ምዕራፍ ፴፰፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ ዓለምን አዲስ ልታደርግ የመጣህ፥ ቅዱስ በሆነው ስምህ አድሰኝ፤ ኅሊናዬ ሆይ ተጓዝ፥ እንደ ለምጻሙ ሰው በመንገድ ቁም፤ እንዲፈውስህም [አዳኝህን] ጥራው፤ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ ለምጻሙንና ሕመምተኛውን፥ ከለምጹና ከሕመሙ  የፈወስከው፥ ከኃጢአት ለምጽና ከቁስሉ ፈውሰኝ። ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ኃጢአቴ ከወዳጆችህ መካከል አሳደደችኝ፤ አንተ ግን በምሕረትህ መልሰኝ፤ ቁስልና ለምጽ ያለበትን ሰው ከከተማ እንዲያስወጡት ሙሴ አዘዘ፤ አንተ ግን በምሕረትህ ፈወስከው፥አስገባኸው፥ ተቀበልከው።ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ ኃጢአቴ አሰደደችኝ፤ አንተ ግን በቸርነትህ ወደ አጸድህ መልሰኝ። 

No comments:

Post a Comment