Monday, December 17, 2012

የስምዖን ዓምዳዊ ጸሎት (ክፍል ሦስት)

ምዕራፍ ፰፡ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ  ሆይ ፥ ሁሉን በማኅፀን የምታበጅ ስትሆን በማኅፀን የተሣልክ፥ ከአባትህና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በኩነታት ያለህ፥ አዲስ ዕቃ እንድሆንና ፈቃድህን ማድረግ እችል ዘንድ በውስጤ ጸጋህን ሳልብኝ። በአንተ እድን ዘንድ ሕይወትንም አገኝ ዘንድ፥ አዲሱን ወይንህን በውስጤ አፍስስ። 

ምዕራፍ ፱፡ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ፥ ከዓለም አስቀድሞ  የአብ ልጅ ስትሆን በሥጋዊ ልደት የተወለድክ፥ አንተን እመስል ዘንድ በመንፈሳዊ ልደት ውለደኝ። 

ምዕራፍ ፲፡ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ፥ ልደትህን በዋሻ ውስጥ ያደረግህ፥ ምስጋናህ በሰማይና በምድር የመላ ሲሆን  ማደሪያ እንደሌለው ደኃ በግርግም ውስጥ የተኛህ፥ ድንቅ የሆነውን ልደትህን እቀበል ዘንድ፥ ሕሊናዬን ዋሻህ አድርገው። ልቡናዬ የመላእክትን መዝሙርና ምስጋና ይማርና ዛሬ መድኃኔ ዓለም ተወልደ፤ ዛሬ በምሕረቱ የሚያሰማራን፥ እንደፈቃዱም የሚመገበን እረኛ ተወለደልን፤ ዛሬ የሕይወት ኅብስት ተዘጋጀልን ተሰጠን ይበል። ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ፥ ሕሊናዬን ለምስጋናህ ማደሪያ በረት እንዲሆን አድርገው። ታላቅ የሆነውን ውበትህን ይየው፤ ነፍሴም ሕይወት ሰጪ የሆነውን መዓዛህን ታሽትተው።  ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ፥ ሕይወት ሰጪ በሆነው በስምህ እርዳኝ፤ ጽኑዕ በሆነው በእጅህም መግበኝ። 


1 comment:

  1. አሜን ! ለአባታችን ቃለ ሔወት ያሰማልን።

    ReplyDelete