Monday, October 31, 2011

ኢየሩሳሌም ኢየሩሳሌም ሉቃ 13:31-35

ፈሪሳውያን ለጌታ ኢየሱስ በማሰብ (አንዳንድ ደግ ፈሪሳውያን አይጠፉምና) ሄሮድስ ሊግድልህ ስለሚፈልግ እባክህ ከዚህ ዘወር በል ብለውት ሲመክሩት እናያለን:: ነገሥታት በምድራዊ ሥልጣናቸው ሥር ብዙ የሚታዘዝ ኃይል ስላላቸው የሚያስፈሩ ሊመስሉ ይችላሉ:: ሆኖም ግን የሥልጣናት ሁሉ ጌታ የሆነው እርሱ ሥልጣን ላላቸው የሚናገር ነው:: በመሆኑም ሄሮድስ በጌታ ኢየሱስ ሕይወት ላይ ሥልጣን እንደሌለውና ነገር ግን በአባቱ ፈቃድና በራሱ ፈቃድ ሞቱ በኢየሩሳሌም እንደሚሆን ይናገራል:: ሆኖም ግን የጌታን ልብ የሰበረው በተንኮሉና በክፋቱ በነፍሰ ገዳይነቱ ቀበሮ የተባለው የሄሮድስ ጌታን ለመግደል መሞከሩ ሳይሆን የኢየሩሳሌም መሲሁንና አዳኟን አለመቀበልዋ ነበር:: ዶሮ ጫጩቶቹዋን ከጭልፊት እንደምትሰውር በክንፎችዋ ከብርድ ሰውራ ሙቀት እንደምትሰጥ ጌታም ኢየሩሳሌምን ከሚመጣባት ፍርድ ለመሰወር ምን ያህል እንደፈለገና ነገር ግን ኢየሩሳሌም የጌታን ፍቅርን ለመቀበል እምቢተኛ እንደሆነች ይነግረናል::

ኢየሩሳሌም የአምላኩዋን ፍቅር እምቢ ብላ መግፋትዋ በስተኋላ በ70 ዓም ፍራሽ በፍራሽ እንድትሆን ልጆቹዋም በመላው ዓለም እንዲበተኑ አድርጎአል:: የጌታንም ልብ የሰበረው ይህ ሊመጣ ያለው የእግዚአብሔርን ፍርድ ለማየት አለመቻላቸው ነበር::

በአመዛኙ በሃይማኖታዊ ህይወታችን ብዙ የምንጨነቀው እግዚአብሔርን የምናስድስትባቸው ብለን ስላዘጋጀናቸው ነገሮች ነው:: ይህ ሁሉ ጥሩ ሆኖ ግን እኛው ባቆምናቸው ህጎች ወጎችና ሥርዓቶች ተውጠን ስንቀር ግን እግዚአብሔር ያዘጋጀልንን መልካም ነገር ለማየት ያቅተናል:: ዋናውን ነገር እንረሳዋለን:: ሌት ተቀን በጾም ሰውነታቸውን የሚያደክሙ ነገር ግን ወንድማቸውን ይቅር ለማለት የማይችሉ ሰዎች ብዙዎች ናቸው:: እንደ አገሬ ደብተራ ማኅሌተ እግዚአብሔርን አደርሳለሁ ብሎ በአምላኩ ፊት ቆሞ እርሱ ግን በዜማው ወዝ ምክንያት ከጓደኛው ጋር በመቋሚያ ይደባደባል:: ዋናውን ነገር መርሳት በትንሹ ነገር ላይ ዋጋ መክፈልን ያመጣል::

አምላኬ ከልቤ ይልቅ ቅርብ እንደሆነ ሳስተውል ከምንም በላይ ላደርግ የሚገባኝ ነገር ቢኖር የእርሱን ፍቅር የእርሱን ምህረት ለመቀበል ልቤን ማዘጋጀት ነው::

No comments:

Post a Comment