Saturday, October 29, 2011

ጌታ ሆይ የሚድኑ ጥቂቶች ናቸውን? ሉቃ 13:22-35

በአገራችን የተለመደ ቀልድ አለ:: ሰውዬው ገሃነም ሲወርድ የንስሐ አባቱን ቀድመው ወርደው ያገኛቸዋል:: ደንግጦ አባቴ እርሶም እዚህ ሲላቸው እርሳቸውም ልጄ ዝም ብል ብፁዕ አባታችንም እዚህ ናቸው በማለት ጳጳሱም እዚህ መሆናቸውን ነገሩት:: ቀልድ ነው ነገር ግን ከፍ ያለ ቁም ነገር የያዘ ቀልድ ነው:: ለምዶብን የእግዚአብሔርን መንግሥት በምድራዊ መመዘኛዎችና በአፍአዊ ድርጊቶች ለማስቀመጥ እንሞክራለን:: በመሆኑም ብዙ ጊዜ በእግዚአብሔር ቤት ሥፍራ የምንሰጣቸው ሰዎች በእግዚአብሔር ዘንድ አንዳችም ቦታ የሌላቸውን ነው:: በዚህ ቦታ ጌታ ከባድ ጥያቄ ተጠይቆአል:: የሚድኑት ጥቂቶች ናቸውን? ጌታ የመለሰላቸው በሁለት መንገድ ነው:: አንደኛ በሩ ጠባብ ስለሆነ ተጋድሎ የሚጠይቅ ነው:: ምን ዓይነት ተጋድሎ ብለን ብንጠይቅ መልሱ በንስሐ ራስን መመርመርና በእግዚአብሔር ጸጋ ላይ መደገፍ ነው:: ሆኖም ግን ብዙዎች ወደዚያ የመዳን ሥፍራ ለመግባት ፈልገው እንደማይሳካላቸው ይነግረናል:: የቃል ኪዳን ልጆች ሆነው ከጸጋው ብርሃን ተቁዋዳሾች የሆኑ ማለትም ቃሉን የሰበኩ የዘመሩ በውጭ ሲጣሉ በአንጻሩ ደግሞ አመዛኙን የእድሜ ዘምናቸውን በኃጢአትና በዝሙት ያሳለፉ አመንዝራዎችና ቀራጮች እነዚያን የሃይማኖት ሰዎች ቀድመው በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ ይገኛሉ:: እድሜ ልካቸውን ስመ እግዚአብሔርን ሲጠሩ የነበሩትን አላውቃችሁም እናንት አመጸኞች ከኔ ወግዱ ሲላቸው እነዚያን ደካሞች የሥነ ምግባር ምስኪኖችን ግን እናንት ቡሩካን ይላቸዋል:: ልዩነቱ ምንድነው ብንል ንስሐ ነው:: ፊተኞች ኋለኞች የሆኑት የተከፈተላቸውን የጸጋና የምህረት በር በሃይማኖተኝነት ትምክሀት በሥሥትና በትዕቢት ስለዘጉት ነው:: ዓይናቸው በሌሎች ሰዎች ኃጢአት ላይ ስለሆነ የራሳቸውን ኃጢአት ለማየት አልቻሉም::

ይህ የጌታ ማስጠንቀቂያ ምን ያሳስበናል? መለስ ብላችሁ እንደገና ጥቅሱን አንብቡት:: ጥያቄው የሚድኑት ጥቂቶች ናቸው ወይ? ነው:: ጥቂት ያደረገው የብዙዎች በቀላሉ መንገድ መሄድ ነው:: ማስመሰል ቀላል ነው:: የባህርይ ለውጥ ከባድ ነው:: የባህርይን ለውጥ ለማምጣት ደግሞ ከባድ ስልሆነብን የመንፈስ ቅዱስ እርዳታ ሊሰጠን ቃል ተገብቶልናል:: በመሆኑም በተከፈተውና ለእኛ በተሰጠን የጸጋና የምህረት ደጃፍ እንለፍ:: በጠባቡ መንገድ እንጋደል::

No comments:

Post a Comment