Wednesday, October 22, 2014

ለቅድስና መረጠን።

Read in PDF

«ዓለም ሳይፈጠር፥ በፊቱ ቅዱሳንና ነውር የሌለን በፍቅር እንሆን ዘንድ በክርስቶስ መረጠን።» 
ኤፌሶን 1፥4 

የመረጠን በፊቱ ቅዱሳንና ነው የሌለን በፍቅር እንሆን ዘንድ ነው። የመጀመሪያውን እንመልከት የመረጠን ቅዱሳን እንሆን ዘንድ ነው። ቅዱስ ማለት ልዩ ንጹሕ ክቡር ማለት ማለት ነው። እግዚአብሔር ቅዱስ ነው። ልዩ ክቡር ንጹሕ ነው።  በነገራችን እግዚአብሔር መንገድ አይደለም በአዲስ ኪዳን የተከተለው። በብሉይ ኪዳንም እስራኤልን ሲመርጥ ያላት ይህን ነበር። «ለእስራኤል ልጆች ማኅበር ሁሉ እንዲህ በላቸው፦ እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ቅዱስ ነኝና እናንተ ቅዱሳን ሁኑ።» ዘሌዋውያን 19፥2  ሌዋውያንን ለመገናኛው ድንኳን አገልግሎት ሲጠራቸው የቅድስና አዋጅን እንዲነግሩ በግንባራቸው ላይ « ቅድስና ለእግዚአብሔር» የሚል ጽሑፍ ያለበት አክሊል እንዲያደርጉ ነበር የነገራቸው።( ዘጸአት 39፥30 ።) በአጠቃላይ እግዚአብሔር እስራኤን የጠራት « ቅዱስ ሕዝብ»  እንድትሆን ነበር። 

በአዲስ ኪዳንም የእግዚአብሔር አሳብ ይኸው ነው። የመረጠን በፊቱ ቅዱሳን እንድንሆን ነው። ቅዱስ ጴጥሮስ ስለዚህ በሚገባ አስረግጦ ይነግረናል። «እናንተ ግን ከጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃኑ የጠራችሁን የእርሱን በጎነት እንድትናገሩ የተመረጠ ትውልድ፥ የንጉሥ ካህናት፥ ቅዱስ ሕዝብ፥ ለርስቱ የተለየ ወገን ናችሁ፤» 1 ጴጥሮስ 2፥9።  ይህን የእግዚአብሔርን ባሕርይ የእኛ ማድረግ የሕይወታችን ነው። ክርስቲያናዊ ሕይወትም የምንለው ይህን ነው። ለዚህም ነው የዕብራውያን ጸሐፊ « ትቀደሱ ዘንድ በብርቱ ፈልጉ ያለ እርሱ ጌታን ሊያይ የሚችል የለምና» በማለት የተናገረው። ዕብራውያን 12፥14። 

እግዚአብሔር ቅዱስ ነው ስንል እግዚአብሔር ብርሃን ነው፥ እግዚአብሔር ፍጹም ነው ማለታችን ነው። እግዚአብሔር ልዩ ክቡር ንጹሕ ነው።  ጨለማ በእርሱ ዘንድ የሌለበት አምላክ ነውና። ይህ የብርሃን ጌታ የቅድስና ሕይወት አሁን እንዳየነው በብሉይም ሆነ በአዲስ ኪዳን ለእኛ ለልጆቹ ሰጥቶናል። የሚያሳዝነው ግን  እኛ ለቅድስና የተጠራን ልጆቹ ስለ ቅድስና ያለን አስተሳሰብ እጅግ ዝቅተኛ ነው። ስለቅድስና ሕይወት ተሰምቶን ያውቃልን? ስለቅድስናችን ሕይወታችንን ለመመርመር ጊዜ ኖሮን ያውቃልን? ቅዱሳን እንድንሆን ልዩ ንጹሕ እንድንሆን እግዚአብሔር ሲጠራን፥ የእርሱ ብርሃንነት በልባችን እንዲያበራና ጨለማ ከእኛ እንዲርቅ ነው። የቅድስና ሕይወት  የልብ ንጽሕና፥ የልብ ብርሃንነት፥ በአሳብ፥ በፈቃድ የመለየት ነው። እግዚአብሔርን የማንገሥ ነገር ነው። በአእምሮ መታደስ ተለውጦ እግዚአብሔርን አክብሮ የመኖርን ሕይወት ነው የሚናገረው። ይህን ነው ቅድስና የምንለው። 

ጳውሎስ ግን በዚህ አያበቃም። የሚለን እግዚአብሔር የመረጠን ቅዱሳንና ነውር የሌለን እንድንሆን ነው። ቅድስና ( ሐጊዮስ) የውስጥ ነገር ነው። ያለ ነውር መኖር  በአፍአ ( በውጭ) ያለ ነገር ነው። በእግዚአብሔርም በሰውም ፊት በቅድስናና ያለ ነውር የመኖር ሕይወት።  በብሉይ ኪዳን እንስሳው ለመሥዋዕት ከመቅረቡ በፊት በሚገባ መመርመር አለበት። ነውር ያለበት እንስሳ ለመሥዋዕትነት መቅረብ አይችልም ነበር። ለእግዚአብሔር የሚቀርበው ጉድለት የሌለበት ከሁሉ የተመረጠውን ነበር።ያለነውር መኖር ማለት ምን ማለት ነው። በቅድስና ሕይወት ለእግዚአብሔር መሰጠት፥ በንጽሕና መኖር፥ ሕይወታችንን እንደፈቃዱ መምራት፥ በሰዎች ፊት ብርሃን መሆን ማለት ነው። ለቤተ ክርስቲያን የተሰጣት ትእዛዝ ይህ ነው። በዓለም ፊት ብርሃን እንድትሆን፥ ጨው እንድትሆን ነው። 

ዛሬ  ቤተ ክርስቲያን (እኛ) በዚያ ውስጥ ነን ወይ? በአገልጋዮቿ መካከል ቅድስና አለ ወይ? በሕዝቦቿ መካከል ያ ቅድስና አለ ወይ? አንድ ታዋቂ የነገረ መለኮት የቅዱሳት መጻሕፍት ሊቅ የተናገረውን እዚህ ጋ ልጥቀስ «  . . . በጥንቷ ቤተ ክርስቲያን ክርስቲያን ከዓለም የተለየ መሆን እንዳለበት ምንም ጥርጥር አልነበረውም። እንዲያውም ልዩነቱ ግልጥ ያለ ስለሆነ፥ ዓለም ሊገድለው ወይም ሊጠላው እንደሚችል ያውቅ ነበር። በዘመናዊው ዓለም ባለችው ቤተ ክርስቲያን ግን በቤተ ክርስቲያንና በዓለም መካከል ያለው ልዩነት እየተድበሰበሰ ነው። እንዲያውም ለሰዎች የምንላቸው « ጥሩና የከበረ ሕይወት እስከኖርክ ድረስ፥ የቤተ ክርስቲያን አባል መሆንና ራስህን ክርስቲያን ብለህ መጥራት ትችላለህ።የግዴታ ከሌሎች ሰዎች የተለየህ መሆን የለብህም።» ዛሬ የብዙዎቻችን ሕይወት ይህ አይደለምን? ዛሬ እኛ በዓለም አደባባይ በቅድስናችን ለእግዚአብሔር ምስክሮች ነን? ያለነውር ነው የምንመላለሰው? አይመስለኝም። 

ክርስቶስ አባቱን ያለው ምንድነው? «እኔ ቃልህን ሰጥቻቸዋለሁ፤ እኔም ከዓለም እንዳይደለሁ ከዓለም አይደሉምና ዓለም ጠላቸው።ከክፉ እንድትጠብቃቸው እንጂ ከዓለም እንድታወጣቸው አልለምንም።እኔ ከዓለም እንዳይደለሁ ከዓለም አይደሉም።» ዮሐንስ 17፥14-16። ቤተ ክርስቲያን ከዓለም እንድትወጣ አይደለም የለመነው፤ እኛም ዛሬ የምንነጋገረው ከዓለም እንድንለይ፥ የሆነ ነገር ዙሪያችንን አጥረን ከዚህ ዓለም ተደብቀን እንድንኖር አይደለም። ነገር ግን ከዓለም ክፋት የተጠበቅን እንድንሆን ነው። ከዓለም ክፋት ተለይተን በቅድስና በእግዚአብሔር ፊት የምንመላለስ።

ያለነውር መኖር ማለት፥ በቅድስና መኖር ማለት ማናቸውንም የሕይወታችንን አቅጣጫ ለእግዚአብሔር ክብር መስጠት ነው። እሁድ ጠዋትን ብቻ ወይም በዓላትን ብቻ ሳይሆን ማናቸውንም የሕይወታችንን አቅጣጫ። ልጆች ስናሳድግ ለእግዚአብሔር ክብር ማሳደግ። የትዳር ሕይወትን ስንመራ ለእግዚአብሔር ክብር መምራት። ሥራችንን ስንሰራ ለእግዚአብሔር ክብር መሥራት። ማናቸውንም ሥራ ቢሆን እጅግ ክቡርን የሆነውን ማቅርብ። አለቃችን ማንም ይሁን ማንም፥ ደመወዛችን ምንም ይሁን ምንም ለእግዚአብሔር ክብር መሥራት። ትምህርታችንን ለእግዚአብሔር ክብር መማር ነው። ያለነውር መኖር ማለት ይህ ነው። 


ታላቁ የነፃነት መሪ ማርቲን ሉተር ኪንግ የባርነት ቀንበር ተጭኖት ለነበረው የጥቁር አሜሪካ ሕዝብ ያለው ይህን ነው። የመከራችሁ ቀንበር ስለበዛ ግድ የለም እንደምንም እንደምንም አድርጋችሁ ኑሩ አይደለም ያለው። ያለውን ልንገራችሁ « ከእናንተ መንገድ ለመጥረግ የተጠራ ቢኖር፥ መንገዱን ሲጠር ፥ ማይክል አንጄሎ እንደሚስል፥ ቤትሆቨን ሙዚቃውን እንደሚያቀናብር፥ ሼክሲፒር ቅኔውን እንደሚደርስ፥ አድርጎ ይጥረግ። የሰማይ ሠራዊት ቆም ብለው « ሥራውን በሚገባ የፈጸመ ታላቅ መንገድ ጠራጊ በዚህ ኖሮ ነበር» ብለው እስኪናገሩ ድረስ መንገድ ጠረጋውን በሚገባ መፈጸም አለበት።» ነውር የሌለበት ሕይወት ይሉሃል ይህ ነው። እግዚአብሔር በሰጠን በማንኛውም የሕይወት ጎዳና ለእግዚአብሔር ክብር መኖር። ከዚህ የበለጠ በቅድስናና ያለነውር መኖር የለም። 

No comments:

Post a Comment