Tuesday, July 9, 2013

ጸሎተ ሃይማኖት (ዘጠነኛ ክፍል)

 Read in PDF

ኮነ ብእሴ ወተሰቅለ በእንቲአነ በመዋዕለ ጲላጦስ ጰንጤናዊ። ሐመ ወሞተ ወተቀብረ ወተንሥአ እሙታን አመ ሣልስት ዕለት በከመ ጽሑፍ ውስተ ቅዱሳት መጻሕፍት። ዐርገ በስብሐት ውስተ ሰማያት ወነበረ በየማነ አቡሁ። ዳግመ ይመጽእ በስብሐት ይኰንን ሕያዋነ ወሙታነ። ወአልቦ ማኅለቅት ለመንግሥቱ።  

ሰው ሁኖ በጰንጤናዊው በጲላጦስ ዘመን ስለ እኛ ተሰቀለ። ታመመ፥ ሞተ ተቀበረም በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፤ በቅዱሳት መጻሕፍት እንደተጻፈ። በክብር ወደ ሰማይ ዐረገ በአባቱም አኝ ተቀመጠ። ዳግመኛ ሕያዋንን ሙታንንም ይገዛ ዘንድ በጌትነት ይመጣል። ለመንግሥቱም ፍጻሜ የለውም። 

1 . ሰው ሁኖ. . . 
የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን በዚህ ምድር መመላለስ በምናሰላስልበት ወቅት ልንዘነጋው የማይገባን ነገር ቢኖር እርሱ በዚህ ምድር የተመላለሰው ፍጹም ሰው ሆኖ ነው። አንዳንድ ሰዎች አምላክነቱን ያገነኑ መስሎአቸው ሰውነቱን ለማሳነስ ይሞክራሉ። ይህን የጸሎተ ሃይማኖት የጥናት ጉዞአችንን ስንጀምር እንዳልነው በክርስትና ትምህርት ላይ በተለይም በነገረ ክርስቶስ (ምሥጢረ ሥጋዌ) እውነት ላይ ከሚነሱት የስህተት ትምህርቶች አንዱ የኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም ሰውነት መካድ ነው። እነዚህም ስሕተቶች ሦስት ዓይነቶች ናቸው፤ አንደኛው « ሥጋውን ከሰማይ ይዞ ወረደ የሚል ነው። ሁለተኛው « ሰው መስሎ ተመላለሰ» የሚል ነው። ሦስተኛው « ሰውነቱን አምላክነቱ ውጦታል» የሚል ነው። ቤተ ክርስቲያን እነዚህን ስህተቶች ፈጽሞ አልተቀበለችውም። ወንጌላውያኑ እንደዘገቡትና ሐዋርያት እንደአስተማሩን ኦርቶዶክሳውያን አባቶቻችንም « ሰው ሆነ» ማለት ብቻ ሳይሆን ይህ ሰው የሆነው ጌታ « የአብርሃም ልጅ» « የዳዊት ልጅ» እንደሆነ መስክረዋል፤ ሐረገ ትውልዱንም ቆጥረዋል። ማቴዎስ 1፥1።  የተዋሃደው የማንን ሥጋ እንደሆነ ቅዱስ መጽሐፍ ሲናገር « የአብርሃምን ዘር ይዞአል እንጂ የያዘው የመላእክትን አይደለም »  ይላል። ዕብራውያን 2፥16።  ስለ ክርስቶስ ፍጹም ሰውነት  መጽሐፍ ቅዱሳችንንን ስናጠና የሚከተሉትን የመጽሐፍ ቅዱስ እውነቶችን እናገኛለን። 
• ከአብርሃም ዘር ከሆነችው ከድንግል የተወለደ፤ ( ማቴዎስ 1፥1 ገላትያ 4፥4) 
• በየጥቂቱ ያደገ ( ሉቃስ 2፥52፤ 4፥16) 
• ሕግን ሁሉ ፈጸመ፤ (ሉቃስ 2፥27፤ ገላትያ4፥4) 
• ተራበ ማቴዎስ 4፥2፤ 21፥18። 
• ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደእኛ ተፈተነ (ዕብራውያን 4፥15) 

2. በጰንጤናዊው ጲላጦስ ዘመን 
ይህ ቁልፍ የሆነ ቃል ነው። በተለይ በዚህ ዘመን፥ ዘመናውያን ምሑራን በ«ታሪካዊው ኢየሱስ» እና « በቤተ ክርስቲያን ኢየሱስ» ማለትም በታሪክ በምናገኘው ኢየሱስ እና ቤተ ክርስቲያን በምትሰብከው ኢየሱስ መካከል ልዩነት እንዳለ በሚሰብኩበት ወቅት፥ የኒው ኤጅ ምሑራን እኛ ሁላችን ኢየሱስ እንደሆን በውስጣችንም ክርስቶስነት እንዳለን በሚነግሩን ወቅት የምናመልከው ጌታ ኢየሱስ ማን እንደሆነ ማወቅ አለብን። የምናመልከው የምንሰግድለት ኢየሱስ በታሪክ የተገለጠውን ኢየሱስ ነው። የአባቶቻችንን ቋንቋ ለመጠቀም የምናመልከው ኢየሱስ « ትንቢት የተነገረለት ሱባኤ የተቆጠረለት ነው።» ወንጌላውያኑ እንደመሰከሩትም (ማቴዎስ 27፥2፤ ሉቃስ 3፥1፤ ሐዋርያቱም እንዳስተማሩት ሐዋ ሥራ 4፥27፤ 1 ጢሞቴዎስ 6፥13) ጌታ በጴንጤናዊው በጲላጦስ ዘመን ስለ እኛ ተሰቀለ።

3. ስለ እኛ ተሰቀለ
እኛን ለማዳን ሲል በሚለው ትምህርታችን ላይ እንደተመለከትነው፥ ጌታ እኛን የሚያድነን ለምን እንደሆነ ተመልክተናል፤ በኃጢአት ስንወድቅ ሁለት ዋና ነገሮች ተከናውኖአል። የእግዚአብሔር ክብር ጎድሎናል። እግዚአብሔር ካዘጋጀልን መንገድ ወጥተን አቅጣጫ ስተናል። (ኃጢአት ማለት መጉደልና አቅጣጫ መሳትም የሆነውም ለዚህ ነው። ) እግዚአብሔር ለእኛ ያዘጋጀልንን ሕይወት ለመኖር ስላልቻልን፥ የእግዚአብሔር ልጅ ከወደቅንበት የኃጢአት አረንቋ ሊያወጣን፥ ሊያድነንና ወደ አባቱ መንግሥት ሊያፈልሰን ወደደ። ይህ ደግሞ የሆነው በመስቀሉ ነው። እዚህ ላይ ልንጠይቀው የሚገባን ነገር ቢኖር መስቀሉ ወይም የመስቀል ሞት ለምን አስፈለገ የሚል ነው። መልሱን የምንገልጠው ጌታ በሥጋዌው ሊያከናውናቸው ከመጣባቸው አገልግሎቶች አንዱ የሆነውን የሊቀ ካህንነቱን ሥራ በመተንተን ነው።
ሊቀ ካህኑ በአገልግሎቱ ውስጥ ሦስት ዋና ዋና ነገሮች አሉት። መሥዋዕት፥ ዕርቅ እና ቡራኬ ናቸው።


መሥዋዕት
በብሉይ ኪዳን ሊቀ ካህኑ በቤተ መቅደስ ከሚያከናውናቸው ነገሮች አንዱና  ዋነኛው መሥዋዕት ማቅረብ ነው። መሥዋዕት በመሠረቱ የዕርቅና የቡራኬ ምክንያት ወይም ምንጭ ነው። ከእግዚአብሔር እርቅ ወይም ቡራኬ የሚፈልግ ሰው ለመሥዋዕት የሚሆን እንስሳ ይዞ የሚመጣውም ለዚህ ነበር። በብሉይ ኪዳን ይቀርቡ የነበሩትን መሥዋዕቶች አሁን በአዲስ ኪዳን ዘመን ላይ ሆነን ስንመለከተው ሊመጣ ያለውን ክርስቶስን ያመለክቱ እንደነበረ እናስተውላለን፤ በዚህም አስተያየታችን ከዕብራውያን ጸሐፊ ጋር እንስማማለን። በዕብራውያን 10 ላይ እንደምናስተውለው እነዚያ ፍጹማን ያይደሉ የብሉይ ኪዳን መሥዋዕቶች ሊመጣ ያለውን ክርስቶስን የሚያመለክቱ ነበሩ። እዚህ ላይ ቆም ብለን እነዚህን የብሉይ ኪዳን መሥዋዕቶች እንመለከታለን።
1. የኃጢአት መሥዋዕት ፤ ባለማወቅ ለሚሠራ ኃጢአት የሚቀርብ መሥዋዕት ነው። ምንም እንኳ የተሠራው ኃጢአት ባለማወቅ የተሠራ ኃጢአት ቢሆንም ሰውየው ከጥፋተኝነት ነጻ ስላልሆነ በእግዚአብሔር ፊት ስለ ኃጢአቱ ካህኑ መሥዋዕት ማቅረብ አለበት። (ዘሌዋውያን 4፥2) መሥዋዕቱ በሚቀርብበት ወቅትም የኃጢአት ይቅርታ ያገኛል። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ ተሸክሞልናል። 1 ጴጥሮስ 2፥24። ይህ የሆነው የእኛን ኃጢአት በመሸከምና ከኃጢአተኞች በመቆጠር ነው። ሮሜ 8፥3፤ 2ቆሮንቶስ 5፥21።
2. የበደል መሥዋዕት፤ ያለማወል ለሚሠራ ኃጢአት ቢሆንም ልዩ የሚያደርገው  « በእግዚአብሔር በተቀደሰው በማናቸው ኃጢአትን ቢሠራ» ለእግዚአብሔር የሚቀርብ መሥዋዕት መሆኑ ነው። ስለ መተላለፍ የሚቀርብ መሥዋዕት ነው። በደለኛው ሰው ወደ ካህኑ የሚያመጣው መሥዋዕት ብቻ ሳይሆን ስለበደሉ የሚሆን ካሣም ነው። ክርስቶስ ስለመተላለፋችን ደቅቆአል። መሥዋዕት ሆኖአል። ኢሳይያስ በትንቢቱ « ስለመተላለፋችን ቆሰለ፥ ስለበደላችን ደቀቀ ይለናል።» ኢሳይያስ 53፥5። በእርሱ መከራና ሞት መተላለፋችን ተወግዶልናል። « መተላለፉ የቀረችለት፥ ኃጢአቱም የተከደነለት ምስጉን ነው» ተብሎ እንደተጻፈ ( መዝሙር 31፥1) ይህን ብፅዕና ለሰጠን ለአምላካችን ክብር ይሁን።
3. የሚቃጠል መሥዋዕት፤ ይህ መሥዋዕት በቤተ መቅደሱ ደጃፍ ላይ ጠዋትና ማታ ለእግዚአብሔር የሚሰዋ መሥዋዕት ነው። ( ዘፀአት 29፥38-42) መሥዋዕቱ ይቀርብ የነበረው ስለ እግዚአብሔር ሕዝብ በአጠቃላይ ሲሆን፤ የአምልኮትና ለእግዚአብሔር የመሠጠት ምልክት ነበር። ከቆዳው በቀር የእንስሳው ሁለንተና እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ የመሥዋዕት ሽታ ሆኖ ይቀርብ ነበር። ጌታም ፍጹም መሥዋዕት ሆኖ በመቅረብ እግዚአብሔርን ደስ አሰኝቶአል። በዮርዳኖስ እግዚአብሔር አብ ሲናገር « በእርሱ ደስ የምሰኝበት» በማለት ተናግሮአል። ማቴዎስ 3፥17።
4. የደኅንነት መሥዋዕት፤ ይህ አንዳንድ ጊዜ የሰላም፥ የምሥጋና የኅብረት መሥዋዕት በመባልም የሚታወቅ ነው። ስያሜው እንደሚያመለክተውም ለምሥጋና የሚቀርብ መሥዋዕት  ነው። አቅራቢዎቹ ካቀረቡት መካከል የሚበሉትም ከዚህ መሥዋዕት ብቻ ነው። ይህ መሥዋዕት ለምስጋና የሚቀርብ መሥዋዕት በመሆኑ ብዙ ጊዜ ሌሎቹ መሥዋዕቶች ከቀረቡ በኋላ የሚቀርብ ነው። በዚህ መሥዋዕት መሥዋዕቱን አቅራቢ ሰው ከሚሠዋው ካህን ጋር እና ቤተሰቡም ካሉ ከቤተሰቡ ጋር በእግዚአብሔር ፊት የመሥዋዕቱን የተወሰነውን ድርሻ በመብላት ከእግዚአብሔር ጋር አንድነታቸውን ያሳያሉ።  ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ከእግዚአብሔር ጋር አንድ ያደርገን ዘንድ ራሱን የሰላም የደኅንነት መሥዋዕት አድርጎ ያቀረበ ነው። ሐሙስ ማታ ሥርዓተ ቍርባንን ሲያሳያቸው ለደቀመዛሙርት ያላቸው « ይህ ጽዋ ስለ እናንተ በሚፈሰው በደሜ የሚሆን አዲስ ኪዳን ነው።» ( ሉቃስ 22፥20) ይህም በኤርምያስ የተነገረውን ቃል የሚያሳስበን ነው። « ከእነዚያ ወራት በኋላ ከእስራኤል ቤት ጋር የምገባው ቃል ኪዳን ይህ ነውና፥ ይላል እግዚአብሔር ሕጌን በልቡናቸው አኖራለሁ፥ በልባቸውም እጽፈዋለሁ እኔም አምላክ እሆናቸዋለሁ እነርሱም ሕዝብ ይሆኑኛል።»  ኤርምያስ 31፥33

ዕርቅ

እንግዲህ እነዚህ ከላይ ያየናቸው መሥዋዕቶች የሚቀርቡት ሰውን በእግዚአብሔር ፊት መተላለፉን ለመደምሰስና ኃጢአቱን ለመክደን ነው። መዝሙር 31፥1።  ካህኑ የመሥዋዕቱን አቅራቢዎች መሥዋዕት ካቀረበ በኋላ እግዚአብሔር መሥዋዕታቸውን እንደተቀበለ፥ በእግዚአብሔር ፊት ይለምንላቸዋል፤ ይጸልይላቸዋል። ያስታርቃቸዋል። የካህኑ አገልግሎት የመካከለኛነት አገልግሎት ነው ያልነው ለዚህ ነው። በብሉይ ኪዳን በብዙ ቦታዎች እንደምንመለከተው በእግዚአብሔር ሕዝብ ዘንድ በደል ሲገኝ ካህኑ በሕዝቡና በእግዚአብሔር መካከል ይቆማል። መካከለኛ የሚለው ቃልም ከዚያ የተገኘ ነው።

በክርስቶስ ስቅለት፥ ሕማምና ሞት ያገኘነውም ይህን ነው። በሥጋው የተቀበለው መከራ የብሉይ ኪዳንን መሥዋዕት እንደሚያሳስቡን ሁሉ፥ ውጤቱም ልክ እንደ ብሉይ ኪዳኑ ዕርቅና ቡራኬ ነው። በክርስቶስ የተገኘው ዕርቅ ግን የተሻለ ዕርቅ ነው።
• እየደጋገመ መሥዋዕት ማቅረብ አያሻውም፤
« እርሱም እንደነዚያ ሊቃነ ካህናት አስቀድሞ ስለ ራሱ ኃጢአት በኋላም ስለ ሕዝቡ ኃጢአት ዕለት ዕለት መሥዋዕትን ሊያቀርብ አያስፈልገውም፤ ራሱን ባቀረበ ጊዜ ይህን አንድ ጊዜ ፈጽሞ አድርጎአልና።» ዕብራውያን 7፥27። 
• የሚሻል ተስፋና የሚሻል ኪዳን ያለው መሥዋዕት ነው። 
« አሁን ግን በሚሻል ተስፋ ቃል በተመሠረተ በሚሻል ኪዳን ደግሞ መካከለኛ እንደሚሆን በዚያ ልክ እጅግ የሚሻል አገልግሎት አግኝቶአል። ፊተኛው ኪዳን ነቀፋ ባይኖረው፥ ለሁለተኛው ስፍራ ባልተፈለገም ነበር።» ዕብራውያን 8፥7። 
• ሕሊናን ማንጻት የሚችል መሥዋዕት ነው። 
ነዚህም እስከ መታደስ ዘመን ድረስ የተደረጉ፥ ስለ ምግብና ስለ መጠጥም ስለ ልዩ ልዩ መታጠብም የሚሆኑ የሥጋ ሥርዓቶች ብቻ ናቸውና የሚያመልከውን በህሊና ፍጹም ሊያደርጉት አይችሉም። . . .የኮርማዎችና የፍየሎች ደም በረከሱትም ላይ የተረጨ የጊደር አመድ ሥጋን ለማንጻት የሚቀድሱ ከሆኑ፥ነውር የሌለው ሆኖ በዘላለም መንፈስ ራሱን ለእግዚአብሔር ያቀረበ የክርስቶስ ደም እንዴት ይልቅ ሕያውን እግዚአብሔርን ልታመልኩ ከሞተ ሥራ ሕሊናችሁን ያነጻ ይሆን?» ዕብራውያን 9፥9 
• አንድ ጊዜ ለዘላለም ለኃጢአት የቀረበ መሥዋዕት ነው።
እንዲሁ ክርስቶስ ደግሞ፥ የብዙዎችን ኃጢአት ሊሸከም አንድ ጊዜ ከተሰዋ በኋላ፥ ያድናቸው ዘንድ ለሚጠባበቁት ሁለተኛ ጊዜ ያለ ኃጢአት ይታይላቸዋል። ዕብራውያን 9፥28። 
• ለሚቀደሱት የዘለዓለም ፍጹማን የሚያደርግ መሥዋዕት ነው። 
«ሊቀ ካህናትም ሁሉ ዕለት ዕለት እያገለገለ ኃጢአትን ሊያስወግዱ ከቶ የማይችሉትን እነዚያን መሥዋዕቶች ብዙ ጊዜ እያቀረበ ቆሞአል፤እርሱ ግን ስለ ኃጢአት አንድን መሥዋዕት ለዘላለም አቅርቦ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀመጠ፥ጠላቶቹም የእግሩ መረገጫ እስኪደረጉ ድረስ ወደ ፊት ይጠብቃል።አንድ ጊዜ በማቅረብ የሚቀደሱትን የዘላለም ፍጹማን አድርጎአቸዋልና። መንፈስ ቅዱስም ደግሞ ስለዚህ ይመሰክርልናል፤ ከዚያ ወራት በኋላ ከእነርሱ ጋር የምገባው ኪዳን ይህ ነው ይላል ጌታ፤ በልባቸው ሕጌን አኖራለሁ በልቡናቸውም እጽፈዋለሁ። ብሎ ከተናገረ በኋላ፥ ኃጢአታቸውንና ዓመጻቸውንም ደግሜ አላስብም ይላል። የእነዚህም ስርየት ባለበት ዘንድ፥ ከዚህ ወዲህ ስለ ኃጢአት ማቅረብ የለም።» ዕብራውያን 10፥ 11-18 


በልጁ በኩል በመታረቃችን  ኃጢአታችን ተሠርዮልናል። 1 ዮሐንስ 2፥12። ኤፌሶን 1፥7። ጸድቅነናል። 1 ቆሮንቶስ 6፥11 ታርቀናል። ሮሜ 5፥1 ተቀድሰናል። 1 ቆሮንቶስ 1፥2። ታትመናል። ኤፌሶን 1፥13፤ 4፥30ልጅነትን አግኝተናል። ዮሐንስ 1፥12፤ ሮሜ 8፥15። ይህ ወደሚቀጥለው ነጥብ ያመጣናል። 

ቡራኬ
በብሉይ ኪዳን ሊቀ ካህናቱ ሕዝቡን ይባርካል። በዘኁልቍ 6፥24 ላይ እንደምናገኘው የአሮን ልጆች የእግዚአብሔር ሕዝብን ሲባርኩ « እግዚአብሔር ይባርክህ ይጠብቅህም፤ እግዚአብሔር ፊቱን ያብራልህ ይራራልህም፤ እግዚአብሔር ፊቱን ወደአንተ ያንሣ ሰላም ይስጥህ።» በማለት ይባርኩ ነበር። ይህ የአሮን በረከት እግዚአብሔር ለሕዝቡ ያለውን ጥበቃ ርኅራኄና ሰላም የሚያመለክት ነው። ይህም በወቅቱ ለእሥራኤላውያን እጅግ የሚያስፈልግ በረከት ነበር። ይህ ግን አሮናዊ በረከት በምድራዊም ሆነ በሰማያዊ በረከት ፍጻሜ ያገኘው በክርስቶስ ነው። ይህ በክርስቶስ ያገኘነው በረከት በሰፊው ተዘርዝሮ የምናገኘው በኤፌሶን 1 ላይ ነው። በጥቅሉ ስናስቀምጠው የአዲስ ኪዳኑ በረከት በክርስቶስ የምንኖረው የእግዚአብሔር ሕይወት ነው። ወይም የአዲስ ኪዳኑ በረከት የእግዚአብሔር መንግሥት ነው።  

1 comment:

  1. Thanks Kesis! It is enlightening. May God bless you more abundantly!

    ReplyDelete