Tuesday, May 14, 2013

ጸሎተ ሃይማኖት (የሃይማኖት ጸሎት)



ነአምን በ፩ዱ፡ አምላክ እግዚአብሔር አብ አኃዜ ኲሉ ገባሬ ሰማያት ወምድር ዘያስተርኢ ወዘኢያስተርኢ። 

ሁሉን በያዘ ሰማይንና ምድርን የሚታየውንና የማይታየውን በፈጠረ በአንድ አምላክ በእግዚአብሔር አብ እናምናለን። 

መቅድም 

ሀ. ስሙ 
1. ጸሎተ ሃይማኖት 
2. የኒቅያ የሃይማኖት መግለጫ (ውሳኔ ሃይማኖት፤ አንቀጸ ሃይማኖት) Nicene Creed 
3. የኒቅያ ቁስጥንጥንያ ውሳኔ ሃይማኖት Nicene-Constantinopolitan Creed

ለ.  ለምን አስፈለገ?
1. « መለኮታዊውንና ሐዋርያዊውን እምነት ጠቅልሎ ያስቀመጠ ስለሆነ።» ቅዱስ አትናቴዎስ 
2. ስለ እግዚአብሔር ባሕርይ መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስተምረውን ግልጥ በማድረግ ከክህደት ምእመናን ለመጠበቅ ነው። 
3. እያንዳንዱ ቃልና ሐረግ የክርስቲያንን እምነት የሚያጠነክር ስለሆነ ነው። 
4. ቤተ ክርስቲያን ልትሆነውና ልታደርገው የሚገባትን ነገር የሚያመለክት ነው። 

ሐ. በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ ያለው ልዩ ቦታ 
1. በመላው የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ተቀባይነት ያለው አንቀጸ ሃይማኖት ነው። 
2 የክርስቶስን አምላክነት የመንፈስ ቅዱስ አምላክነት  በማብራራት ቤተ ክርስቲያንን ከታላቅ አደጋ የታደገ ነው።   
3. በኒቅያ በ325 ዓ.ም ላይ   እንደገና በ381 ዓ.ም ላይ በቁስጥንጥንያ በተከናወነው ኢኩሜኒካል ጉባኤ ላይ ተጨማሪ አንቀጾች ( መንፈስ ቅዱስን የሚመለከቱ) ገብቶለት ቤተ ክርስቲያንን በቀጥተኛ ሃይማኖት (ኦርቶዶክስ) የመራ ነው። 

መ. በቤተ ክርስቲያን የአምልኮ ሕይወት ያለው ቦታ
1. በጸሎት ማለትም በቅዳሴ ጊዜ በካህናትና በምእመናን ይደገማል። 
2. የሚጠመቁ ሰዎች እምነታቸውን የሚገልጡት ጸሎተ ሃይማኖትን አሰምተው በመድገም ነው። (የክርስትና አባትና እናት ስለሕፃኑ ፈንታ ሁነው በጸሎተ ሃይማኖት እምነታቸውን መመስከር አለባቸው።  
3. የክርስትና መለያ ምልክት ስለሆነ በምኩራብ የእምነት መግለጫ የሆነው « እስራኤል ሆይ ስማ (ሼማ)በሚለው የአይሁድ አንቀጸ ሃይማኖት ትይዩ ሊታይ የሚችል ነው። 

መ. ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር ያለው ግንኙነት 
1. ጸሎተ ሃይማኖት በተደነገገ ወቅት ገና የመጽሐፍ ቅዱስ ቀኖና ገና አልተቋጨም ነበር። 
2. ጸሎተ ሃይማኖት ብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶችን የያዘ ስለሆነ የመጽሐፍ ቅዱስ ቀኖና ለመወሰን ማለትም የትኞቹ መጻሕፍት በቅዱሳት መጻሕፍት ቁጥር መግባት እንዳለባቸው ለመወሰን አገልግሎአል። 


ክፍል አንድ 
ነአምን በአሐዱ አምላክ እግዚአብሔር አብ


ሀ. እናምናለን።  (ነአምን) 

እምነት ደረቅ የሆነ የመረጃ ጥርቅም ሳይሆን በሕይወታችን ውስጥ ለውጥ የሚያመጣ የመዳን መንገድ ነው። እናምናለን የምንለው እውነት በጸሎታችን፥ በክርስቲያናዊ ሕይወታችን ውስጥ እንዴት ባለ መንገድ መመራት እንዳለብን የሚያሳስብ ነው። የሰውን ሁለንተና የሚነካ ነው። 

• እምነት አእምሮን ይዛል፤ በመሆኑም « ሁሉን በያዘ ሰማይና ምድርን የሚታይና የማይታየውን በፈጠረ በአንድ አምላክ እናምናለን» ብለን ስንናገር፥ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ዓለምን የምናየው በተለየ መንገድ ነው። 
• እምነት ፈቃድን ይይዛል፤ እምነት ማለት በፈቃዳችን ወደ እኛ ለቀረበው ለእግዚአብሔር መስጠታችን ነው። 
• እምነት ስሜትን ይይዛል፤ እምነት ማለት ላዳነን ለእግዚአብሔር የምንሰጠው የፍቅር ምላሽ ነው። ይህ ለእግዚአብሔር ያለን ፍቅር ደግሞ ሌሎችን በመውደድ ይገለጣል። 

በመሆኑም እምነት አራት መልካም ነገሮችን በክርስቲያን ሕይወት ውስጥ ያከናውናል። 

1. አንደኛው በእምነት በኩል ነፍስ ከእግዚአብሔር ጋር አንድነት ይኖራታል። ሆሴዕ 2፥2። 
እምነት ሳይኖረው ማንም ሰው በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት አይኖረውም። (ማር 16፥16) 
ያለእምነት የሆነ ነገር ሁሉ ኃጢአት ነው። ሮሜ 14፥23 
« ዘላለማዊውንና የማይለወጠውን እውነት ማወቅ በሌለበት ሥፍራ በመልካም ምግባር የተጌጠ ሕይወት እንኳ ሐሰት ሊሆን ይችላል።» አውግስጢኖስ። 



2. ሁለተኛው የእምነት ውጤት የዘላለም ሕይወት ነው።
ያለ እግዚአብሔርን ማወቅ የዘላለም ሕይወት ምንም ማለት አይደለም። ዮሐ 17፥3። ይህ እግዚአብሔርን ማወቅ የሚጀምረው በእምነት በኩሉ አሁን በዚህ ምድር ሳለን ነው።  ይህ እውቀት ፍጹም የሚሆነው ግን እግዚአብሔርን በሙላቱ ስናውቀው ወደፊት ነው።  እምነት ተስፋ የምናደርገውን ነገር የሚያስረግጥ ነው። ዕብራውያን 11፥1። በመጀመሪያ እግዚአብሔርን በእምነት በኩል ሳያውቀው ማንም ሰው ፍጹም ወደሆነው ወደሰማያዊ ደስታ እርሱም ወደ እውነተኛው እግዚአብሔርን ማወቅ መድረስ አይችልም። « ሳያዩኝ የሚያምኑኝ ብፁዓን ናቸው። ዮሐንስ 20፥29። 


3. ሦስተኛው ከእምነት የሚገኝ መልካም ነገር ለዛሬው ሕይወታችን ትክክለኛውን አቅጣጫ ይሰጠናል ወይም ያመላክተናል።
አንድ ሰው መልካም ኑሮ ለመኖር፥ በትክክለኛ መንገድ ለመኖር የሚያስፈልገው ነገር ምን እንደሆነ ማወቅ አስፈላጊ ነው ። ይህን ለማወቅ ደግሞ በራሱ ጥረት ብቻ የሚደገፍ ከሆነ፥ ይህን እውቀት ሊያገኝ አይችልም ወይም ብዙ ድካም ይጠይቅበታል። እምነት ግን መልካም ሕይወትን እንዴት መኖር እንደሚቻል ያስተምረናል። « ጻድቅ በእምነት ይኖራል።» ያዕቆብ 2፥4። 


4. አራተኛው የእምነት ውጤት በእምነት ፈተናን ድል እናደርጋለን። 
« በእምነት ቅዱሳን መንግሥታትን ድል ነሡ» ዕብራውያን 11፥33። ማናቸውም ፈተና  ከዓለም ወይም ከሥጋ ወይም ከዲያብሎስ ነው። ዲያብሎስ ለእግዚአብሔር ከመታዘዝ ይልቅ እንድናምጽበት ይሻል። 1 ጴጥሮስ 5፥8። ዓለም ደግሞ በብልጥግናዋ ከእርሷ ጋር እንድንጣበቅ በማድረግ ወይም ደግሞ በባላጋራነት በማስፈራራት ትፈትነናለች። ነገር ግን እምነት ግን የሚመጣውን እና የተሻለውን ሕይወት በማመን ይህን ድል ያደርገዋል።  « ዓለምንም የሚያሸንፈው እምነታችሁ ነው። 1 ዮሐንስ 5፥4። ሥጋ ደግሞ በአንጻሩ የሚፈትነን ቶሎ ወደሚያልፉት የአሁኑ አለም እርካታዎች እንድንሳብ በማድረግ ነው። ነገር ግን እምነት ደግሞ በእነዚህ ጊዜያዊ ነገሮች ላይ ብንጠለጠል ዘላለማዊውን ደስታችንን እንደምናጣ ያሳየናል። « በሁሉም ነገር የእምነትን ጋሻ ውሰዱ። 

ለ. በአንድ አምላክ በእግዚአብሔር አብ  (በአሐዱ አምላክ እግዚአብሔር አብ )

በክርስትና እምነታችን ውስጥ ዋናውና ማዕከላዊው ነጥብ ምሥጢረ ሥላሴ ነው።
አንድ ሊቅ ሲናገር « ምሥጢረ ሥላሴን ካድ፥ መዳንህን ታጣለህ፤ ምሥጢረ ሥላሴን ጠቅልለህ ለማወቅ ሞክር አእምሮህን ታጣለህ።» ብሎአል።

1. ምሥጢረ ሥላሴን በሚገባ መረዳት የምንችለው እግዚአብሔር  በቃሉ ማለትም በቅዱሳት መጻሕፍት ራሱን የገለጠበትን መንገድ በመረዳት ነው።

• የእግዚአብሔር አንድነት በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ተብራርቶ ተጠቅሶአል። ዘዳግም 6፥4-5፤ 2 ሳሙኤል 7፥22፤ ኢሳይያስ 45፥18።
  • የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት በአዲስ ኪዳን ጸሐፊዎች ተብራርቶ ተገልጧል። ዮሐንስ 1፥1፤ 20፥28፤ ሮሜ 9፥5፤ ቲቶ 2፥13፤ቅ
• ቃል በመጀመሪያ እንደነበረ፤ (ዮሐንስ 1፥1፤ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ እንደነበረ  ዮሐንስ 1፥1፤ ቃልም እግዚአብሔር እንደሆነ (ዮሐንስ 1፥1) ቃልም ሥጋ እንደሆነ (ዮሐንስ 1፥14) ያ ቃል (ልጁ) በአባቱ ዘንድ ያለውን እንደተረከልን (ዮሐንስ 1፥18) ያስተምረናል። 
• መንፈስ ቅዱስ በክርስቶስ ባመኑት ላይ ማደሩና ቤተ ክርስቲያንን መምራቱ በሰፊው በአዲስ ኪዳን ተገልጧል። ዮሐ 14፥15-17።

  1. ይህ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተገለጠው እውነት የሚያሳየን እውነት ምንድነው።

•  እግዚአብሔር በአንድነቱ አለ።
• እግዚአብሔር በሦስትነቱ አለ። ይህ አንዱ እግዚአብሔር ሦስት አካላት ማለትም አብ፥ ወልድ፥ መንፈስ ቅዱስ ነው። ሦስቱም አካላት በመለኮት አንድ ስለሆኑ አብ እግዚአብሔር ነው፤ ወልድ እግዚአብሔር ነው። መንፈስ ቅዱስ እግዚአብሔር ነው። በአንድነቱ ውስጥ ሦስትነቱ አለ። በሦስትነቱ ውስጥ አንድነቱ አለ።
• እነዚህ ሦስቱ አካላት በሥማቸው እና በግብራቸው አንዳቸው ከሌላቸው ልዩ ናቸው።
አብ በአባትነቱ አብ ተብሎአል። ወልድ በልጅነቱ በልደቱ ወልድ ተብሎአል። መንፈስ ቅዱስም ከአብ የወጣ በመሆኑ ከአብ የወጥ ( ሠራፂ) ተብሎአል።

ቤተ ክርስቲያን በጸሎቱዋ « ለአብ፥ ለወልድ፥ ለመንፈስ ቅዱስ እሰግዳለሁ፤ አንድ ሲሆኑ ሦስት፤ ሦስት ሲሆኑ አንድ፥ በአካል ሦስት ሲሆኑ በመለኮት አንድ ለሚሆኑ» በማለት ይህን የመጽሐፍ ቅዱስ እውነት በእምነት ትመሰክራለች። (ጸሎት ዘዘወትርን ተመልከት።
  1. ቤተ ክርስቲያን ጸሎትዋ የምሥጢረ ሥላሴ ትምህርቷን የሚያመለክት ነው።

• ጸሎታችንን የምናቀርበው ወደአብ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በመንፈስ ቅዱስ አማካኝነት ነው።
 ___ አባታችን ሆይ ብለን እንጸልያለን።
___ በእንድ ልጅህ በኢየሱስ ክርስቶስ ብለን በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እንጸልያለን።
___ በመንፈስ ቅዱስ ተመልተንና ተመርተን እንጸልያለን።

  1. ቤተ ክርስቲያን ሕይወቷ ምሥጢረ ሥላሴን የሚያመለክት ነው።

• ምሥጢረ ሥላሴ የሚያስተምረን የመጀመሪያው እውነት የእኛ ማንነት ያለው ከክርስቶስ አካል ጋር ባለን ሕይወት እንጂ በግለኝነት በሚኖረን ሕይወት አይደለም።
• ሁለተኛው ትምህርት እግዚአብሔር ፍቅር ነው። የእግዚአብሔር ፍቅርም በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ መካከል እንዲሁም ለፍጥረቱ በሙሉ እግዚአብሔር ባለው ፍቅር ታይቶአል። ይህ ፍቅር በሥላሴ የምናምን እኛም ለፍጥረት ሁሉ ፍቅርን እንድገልጥ ያስተምረናል።


ለሚከተሉት ጥያቄዎች መልስ ስጡ



1. ጸሎተ ሃይማኖት በስንት ዓ. ም ተወሰነ?ለምንስ ጸሎተ ሃይማኖት ተባለ? ሌላ ስሙስ ማን ይባላል? 

2. የጸሎተ ሃይማኖት አከፋፈል እንዴት ነው? 

3. እምነት በሕይወታችን ውስጥ  ምን ዓይነት ፍሬ ያፈራል? 

4. ስለ ምሥጢረ ሥላሴ መጽሐፍ ቅዱስ ምን ያስተምራል? 

5. ስለ እግዚአብሔር ወልድ  ወይም ስለእግዚአብሔር ቃል በተብራራ መልኩ የምናገኘው በየትኛው ወንጌል ነው። ምዕራፍና ቁጥር ጥቀሱ። 

6. ሥላሴን መርምረን በምልዓት ልንረዳ እንችላለን ወይ? አብራሩ። 

1 comment: