Tuesday, March 30, 2010

በመከራችን የቀረበን አምላክ


ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደ እኛ የተፈተነ ነው እንጂ፥ በድካማችን ሊራራልን የማይችል ሊቀ ካህናት የለንም።
16 እንግዲህ ምሕረትን እንድንቀበል በሚያስፈልገንም ጊዜ የሚረዳንን ጸጋ እንድናገኝ ወደ ጸጋው ዙፋን በእምነት እንቅረብ። ዕብ 4፥15-1

በዚህ ሰ ሙነ ሕማማት አንዱ ልናሰላስለው የሚገባን ነገር ቢኖር አምላካችን ምን ያህል በመከራችን የቀረበን አምላክ መሆኑን ነው። በሰማይ ያለፈ ታላቁ ሊቀ ካህናችን፥ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የሚመለክና የሚሰገድለት፥ በሌላ በኩል ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደእኛ የተፈተነ ነው። ይህ ቃል ለሕይወቴ ሦስት ዓበይት መልእክቶች አሉት።

1 የምጓዝበትን መንገድ የሚያውቅ አምላክ አለኝ። አንዳንድ ጊዜ በዚህ ዓለም ጉዞአችን ውስጥ አስቸጋሪው ነገር የሚረዳንን ሰው ማግኘቱ ነው። ጣት የሚጠቁም፥ ደካማ ጎናችንን የሚዳስስ፥ እንዲህ አድርግ እንዲያ አታድርግ የሚል ማግኘቱ ላይ ችግር የለብንም። ነገር ግን የልባችንን ስብራት የሚያውቅ፥ ውስጣዊ ነገራችንን የሚገነዘብ ማግኘት ከባድ ነው። በሌሎች ሃይማኖቶች አምላክ ከሰው በጣም የራቀ ነው። በክርስትናችን ደግሞ አምላክ ከመቅረብ አልፎ አንድ ሆኖአል። እንደ እኛ ተፈትኖአል። ይህ ወደሚቀጥለው ክፍል ያመጣኛል።

2 የምጓዝበትን መንገድ የሚያውቅ ብቻ ሳይሆን በጉዞዬ ባልደረባ የሚሆን አምላክ አለኝ። ዛሬ ይህን አረፍተ ነገር ስጽፍ ልቤ የከበደበት ነገር ነበረ። ነገር ግን ይህን ቃል እንዳስብ መንፈስ ቅዱስ መራኝ። <እንደ እኔ የተፈተነ> አምላክ አለኝ። የተገፋ፥ መከራ የደረሰበት፥ የተጠማ፥ የተናቀ አምላክ አለኝ። የሚሰማኝን ያውቀዋል። የልቤን ቁስለት ያውቀዋል።

3 እኔ የማልፍበትን ውጣ ውረድ የሞላበትን የሕይወት ጎዳና ስለሚያውቅ፥ አምላኬ ለእኔ ያለው ርህራሄ ታላቅ ነው። የማይራራ ሊቀ ካህን የለንም። ሐዘንን የቀመሰው ያውቀዋልና።
በሌላ አነጋገር ይህ ሰሞን አምላካችን የእኛን መንገድ ምን ያህል እንደተጉዋዘ የምናይበት ወቅት ነው። ክርስቶስ ስለኃጢአታችን ሞተ ስለ በደላችን ደቀቀ የሚለው ቃል ህያው የሆነ ለኑሮአችን ልዩ ትርጉም ያለው ቃል ነው።

ስለዚህ ወንድሞቼና እህቶቼ ብቻችንን አይደለንም። አዳኛችን የቀረበን ህዝቦች ነን። ህይወት አስቸጋሪ ወደሆኑ ድንበሮች ቢወስደን ያለንበትን ሁኔታ ከማንም በላይ የሚያውቅ አምላክ እንዳለን እናስተውል። ይቆየን።

No comments:

Post a Comment