Monday, March 29, 2010

ሰሙነ ሕማማት የመስቀሉ ውለታ

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች < እኛ የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን> በማለት በመስቀሉ የተከናወነው አስደናቂ ምሥጢር የክርስትናችን ዋና መልእክት እንደሆነ ገልጦአል። 1 ቆሮ1፥ 23። ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ሊገልጥላቸው የፈለገው፥ ከአይሁድ ምልክት (ተአምር)ከግሪኮች ጥበብ (ፍልስፍና) በላይ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ በመስቀል ላይ ያሳየን ፍቅር አስደናቂ መ,ሆኑን ነው። ሐዋርያው ዮሐንስ ስለዚህ ፍቅር ሲናገር <በዚህ የእግዚአብሔር ፍቅር በእኛ ዘንድ ተገለጠ፥ በእርሱ በኩል በሕይወት እንኖር ዘንድ እግዚአብሔር አንድ ልጁን ወደ ዓለም ልኮታልና።ፍቅርም እንደዚህ ነው፤ እግዚአብሔር እርሱ ራሱ እንደ ወደደን ስለ ኃጢአታችንም ማስተስሪያ ይሆን ዘንድ ልጁን እንደ ላከ እንጂ እኛ እግዚአብሔርን እንደ ወደድነው አይደለም።> በማለት አምላካችን በመስቀል ላይ መከራ የተቀበለው ለእኛ ካለው ፍጹም ፍቅር የተነሳ እንደሆነ አስተምሮናል። ቤተ ክርስቲያናችን ከትንሣኤ በፊት ባለው ሳምንት ይህን ይህን የጌታን ህማምና መከራ ታስታውሳለች። ሳምንቱንም ሰሙነ ሕማማት (Passion Week) ብላ ትጠራዋለች። በዚህ ሳምንትም ቤተ ክርስቲያናችን ምዕመናንን ለስግደት ለጾምና ትጠራለች። በየዕለቱም ጌታ ከመሰቀሉ በፊት ባሉት አምስት ቀናት የተከናወኑትን ድርጊቶች የሚያወሱ ምንባባት ከብሉይ ኪዳን ከአዲስ ኪዳን ከኦርቶዶክሳውያን አባቶች መጻሕፍት በማውጣጣት ይነበባል። እነዚህን የቅዱሳት መጻሕፍት አስተዋጽኦ የያዘውና ሳምንቱን በሙሉ የሚነበበው መጽሐፍ ግብረ ሕማማት ይባላል። ግብረ ሕማማት በሚነበብበት ወቅት በሰባቱ ሰዓታት ቁጥር የክርስቶስን ሕማምና መከራ በማሰብ ስግደት ይደረጋል፤ መዝሙር ይዘመራል። በቤተ ክርስቲያን የሚከናወነው ሥርዓት በሙሉ ፍጹም ምሳሌያዊ በመሆኑ ምዕመናን በእግረ ሕሊናቸው ወደ ቀራንዮ ይሄዳሉ፤ አምላካቸው ለእነርሱ ያደረገውን በማስተዋል ያመሰገኑታል፥ ያመልኩታል፥ ያከብሩታል። የሰውንም ጠንካራ ልብ በማሰብ፥ ሰው በአዳኙ በቤዛው ላይ ያደረገውን ጭካኔ የተሞላበትን ድርጊት በማሰብ ያዝናሉ፥ የራሳቸውንም የልብ ጥንካሬ በማሰብም አምላክ ሆይ በፍቅርህ ሙላኝ በምህረት አስበኝ ይላሉ።
ለዚህም ነው ስምዖን ዐምዳዊ በጸሎቱ እንዲህ ያለው፤
በመስቀል ላይ እንዴት እጅህን ዘረጋህ እንዴትስ በቀኖት ተቸነከርክ? ወዴትስ ወረድክ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ፍቅርህን በልቤ ውስጥ ቅረጽ ከክፉ ማሰሪያ ፍታኝ፤ ለዘላለም በሚኖረው ፍቅር እሰረኝጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ማሕየዊ መስቀልህን አቅፌ ከእርሱ የሕይወትና የመድኃኒት መዐዛ እንዳሸት አድርገኝ፤በልቡናዬም ውስጥ ንጹሕ ደምህ ይውረድ ንጹሕ መሠዊያ ይሆን ዘንድ ልቡናዬን ያክብረው፤ በውስጡም የሕይወት መንፈስ ይንቀሳቀስ፤ የሕይወትንም መንፈስ አንተን ይቀበል።

No comments:

Post a Comment