Friday, December 20, 2013

ጋብቻና ድንበር (ወሰን)

ቀሲስ ዳውድ ላሜይ ( ካይሮ ቅዱስ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያን)
ትርጉም በሊ.ኅ.መ.ባ 

Read in PDF
ጋብቻችን በክርስቶስ የተጠበቀ እንዲሆን ከውጭው ዓለም ጋር በሚኖራችሁ ግንኙነት ላይ ድንበር ወይም ወሰን ማስቀመጥ መቻል አለባችሁ። ብዙ ጋብቻዎች ወደብዙ ችግር የሚገቡት፥ በእነርሱና በቤተሰቦቻቸው፥ በእነርሱና በአማቾቻቸው፥ በጓደኞቻቸው፥ በሥራ ባልደረቦቻቸው ሌላው ቀርቶ እርስ በእርሳቸው ባላቸው ሕይወት ይህን አስፈላጊ የሆነ ድንበርና ወሰን ለማስቀመጥ ባለመቻላቸው ነው። 

እናንተና የትዳር ጓደኛችሁ ወሰንና ድንበር የማታስቀምጡበት አንድ ነገር ቢኖር  ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ያላችሁ ሕይወት ነው። እናንተ [በፈቃዳችሁ ካልሆነ] ከማንም ጣልቃ ገብነት የተጠበቃችሁ በራሳችሁ ምሉዓን የሆናችሁ ሰዎች ናችሁ። 

ይህ ማለት ግን ራሳችሁን ሙሉ በሙሉ ከውጫዊው ዓለም መለየት አለባችሁ፤ በተባሕትዎ በብቸኝነት መኖር አለባችሁ ማለቴ አይደለም። ለማለት የፈለግሁት ከማናቸው ሰው ጋር የሚኖራችሁ ግንኙነት በጋብቻ ሕይወታችሁ ውስጥ ጣልቃ እንዳይገባ እንድትጠነቀቁ ይገባል ነው።

ቤተ ክርስቲያን ከእግዚአብሔር ቃል የሚከተሉትን ምንባባት መርጣ የሚጋቡትን የምታሳስበው እንዲያው በግብታዊነት አይደለም። 
« ስለዚህ ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል፥ ከሚስቱም ጋር ይተባበራል፥ ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ» ማቴዎስ 19፥5። 
« ልጄ ሆይ፥ ስሚ እዪ ጆሮሽንም አዘንብዪ ወገንሽን ያባትሽንም ቤት እርሺ» መዝሙር 45፥10። 

ስለራሳችን ስለቤተሰቦችንና ስለወላጆቻችን መንፈስ ቅዱስ እንዲህ ያለ ምክር ከሰጠን፥ ከሌሎች ጋር ስላለንም ግንኙነት እንደዚሁ ልንጠነቀቅ እንደሚገባ የታወቀ ነው። 

« ወገንን የአባትን ቤት መርሳት» ወይም « አባትንና እናትን መተው» ማለት ምን ማለት ነው? 

መርሳት ወይም መተው ማለት ከጋብቻ በፊት እንደገፍባቸው ግንኙነቶችን «በመጣል»  ወደ ሌላ አቅጣጫ ትኩረትን ማድረግ ማለት ነው። የሚያስገርመው ከተወለደበት ጊዜ ጀምሮ ከአባቱና ከእናቱ ጋር እንደነበረው ያለ ጠንካራ ግንኙነት ከጋብቻ በኋላ ከሚስቱ ጋር ሊኖረው እንደሚገባ በአጽንኦት ለመግለጥ፥  መንፈስ ቅዱስ « አባትና እናቱን ይተዋል» ካለ በኋላ « ከሚስቱም ጋር ይተባበራል( ይጣበቃል)» አለ። ይህ ግንኙነት ከአባትና ከእናቱ ጋር ከነበረው ግንኙነት የተለየ ነው፤ ይህ ግንኙነት እስከ ሕይወት ፍጻሜ የሚዘልቅ ግንኙነት ነው። 

መተው (መጣል) 

መተው ( መጣል) ከዚህ ዓውደ ንባብ አንጻር በሚገባ የሚገልጠው ሕፃናት ልጆች ምግባቸውን ለማግኘት የእናታቸውን ጡት ሙሉ በሙሉ መደገፋቸውን ትተው ወደ ሚቀጥለው ደረጃ ማለትም ምግባቸውን ከሌላ ሥፍራ ለማግኘት የሚያደርጉትን ሂደት ያመለክታል። ( ጡት ጣለ ( ተወ) የሚለውን የአገራችንን አባባል ያመለክቷል) 

መተው ( መጣል) የሚለው ቃል በራስ የመቆምንና የማንነትን አሳብ ያዘለ « ነፃነትን» የሚያመለክት ነው። ቀላል ሂደት አይደለም። በመጀመሪያ በጣም አስቸጋሪ ይሆናል። አስቸጋሪነቱ ለሕፃኑ ብቻ ሳይሆን ለእናትም ነው። ጡቱ መጥባቱን ሲተው እናት ሕፃኑ ከእርሷ ጋር ያለውን ቀረቤታ እንደተወ እና እንዳስለመደው በእርሷ መደገፉን እንዳቆመ ይሰማታል። 

መተው ( መጣል) ልጆች ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ትምህርት ቤት ሲሄዱም ይታያል። ከወላጆቿቸው ሊለዩና ለረጅም ጊዜ ያለ እነርሱ ሊቆዩ መሆኑን ሲያውቁ ምርር ብለው ያለቅሳሉ። በተመሳሳይ መንገድ ሰው በጋብቻ ሕይወት ውስጥ ሲገባ ሌላው መተው ( መጣል) ይከሰታል። 

በእኛ ባህል « መተው» ሁል ጊዜ እንዲዘገይ ይደረጋል። እናቶች ልጆቻቸውን ከሁለት ዓመት በላይ ዕድሜ ኖሮአቸው ለማጥባት ይፈልጋሉ።. . . 

ተጋቢዎች ከወላጆቻቸውና ከዘመዶቻቸው ጋር ያላቸውን « የመተው» ሂደት በጊዜ ካላደረጉት፥ በጋብቻ ሕይወታቸው ውስጥ ብስለትና ነጻነት ያለበት የአብሮነት ሕይወትን ለመኖር የማይችሉበት ነጥብ ላይ ይደርሳሉ። 

ይህ ቤተሰቦቻችንን የመተው ሂደት ልክ እንደሌሎቹ ሂደቶች ( ጡት እንደመተው፥ ትምህት ቤት እንደመግባት) አስቸጋሪና ለመጀመሪያ ከፍተኛ ሕመም የሚፈጥርብን ነው። ነገር ግን በጋብቻ ሕይወታችን ለማደግና ለመጠንከር ግዴታ ነው። በመሆኑም ይህን የነጻነት ኑሮ ለመኖር ከወሰኑበት ወቅት ጀምሮ ይህን ውሳኔአቸውን በተመለከት ሊመጣባቸው የሚችለውን ፈርጀ ብዙ የሆኑ ፈተናዎች በጋብቻ ሕይወት የሚኖሩ ሰዎች ከእጮኝነት ሕይወታቸው ጀምሮ በሚገባ ሊገነዘቡት ይገባል። 

« ድንበር ማስቀመጥ» ማለት ሁለቱ ምክር ፈልገው ከሚቀርቡአቸው ንስሐ አባትና የጋብቻ አማካሪዎች  ውጭ የሁለት ባለትዳር ጓደኞች ግላዊ ሕይወት በሌሎች ሊደፈር አይገባም ማለት ነው።  በጋብቻ ያሉ የባልና የሚስት ዝርዝር የትዳር ሕይወት በወላጆች፥ በቤተሰብ አባላት፥ በጓደኞችና በቤተ ዘመዶች መካከል የወሬ ርእስ መሆን የለበትም። 

አንዳንድ ወላጆች የእነርሱ ጣልቃ ገብነትና ስለልጆቻቸው ጋብቻ የሚሰጡት አስተያየት በልጆቻቸው የጋብቻ ሕይወት ላይ ምን ያህል አደገኛ ተጽዕኖ እንደሚኖረው አያስተውሉም። ልጆቻቸው የጋብቻ ሕይወታቸውን ለመጠበቅ ያስቀመጡትን ድንበር ወይም ወሰን ለማክበር  አንዳንድ ወላጆች በጣም ይቸግራቸዋል፤ ፈቃደኞችም አይደሉም። ልጆቻቸው ለእነርሱ ምንም እንደማያስቡና ታማኞች እንዳይደሉ አድርገው ቅሬታ ያሰማሉ። ያለመታደል ሆኖ ብዙዎች ባሎችና ሚስቶች በዚህ የጥፋተኝነት ስሜት ስለሚሰማቸው ወደዚህ ወጥመድ ይወድቁና በጋብቻ ሕይወታቸው ያለባቸውን ኃላፊነት ወደጎን በማድረግ የወላጆቻቸውን ፍላጎት ለማርካት ይሞክራሉ። 


ለወላጆቻችሁ ያላችሁን ታማኝነትና ለትዳራችሁ ያላችሁን ኃላፊነት ሚዛናዊ ማድረግ ለጋብቻ ሕይወታችሁ ዕድገትና ስኬት እጅግ አስፈላጊ ነው። በመልካም ትህትና፥ ለእናታችሁ ወይም ለአባታችሁ መቼና እንዴት « አይሆንም፤ አይደረግም» ማለት እንዳለባችሁ ማወቅ፤ ከትዳር ጓደኛችሁ ጋር ያላችሁ ሕይወት ቅድሚያ ለመስጠት መወሰን ፤ ከሁሉም በላይ « አባትና እናታችሁን ተዉ፤ ከትዳር ጓደኛችሁ ጋር ተባበሩ» ላለው ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ለመታዘዝ ከሁሉ በፊት ቅድሚያ ለመስጠት መወሰን እጅግ አስፈላጊ ነገር ነው።  

የስምዖን ዓምዳዊ ጸሎት (ካለፈው የቀጠለ)


Thursday, December 19, 2013

ትዳርና አመለካከት

በቀሲስ ዳውድ ላሜይ  ( ካይሮ ቅዱስ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያን) 
ትርጉም በሊ.ኅ.መ.ባ
በጋብቻ ውስጥ ደስታን ለማግኘት የመጀመሪያው ቁልፍ ነገር ባልና ሚስት የሚኖራቸው « አመለካከት» ነው። በትዳር ውስጥ ያለ አመለካከት ባልና ሚስት አንዳቸው ሌላቸውን፥ የራሳቸውን ሕይወትና በዙሪያቸው ያሉትን በሚመለክቱበት እይታ ላይ የተመሠረተ ነው። በራስ ሕይወት፥ በትዳር ጓደኛ፥ እኛን አንድ አድርጎ ባያያዘን ግንኙነትና በአጠቃላይ በሕይወት ውስጥ አዎንታዊ የሆነ ክርስቲያናዊ አመለካከትን ማዳበር ለጋብቻችን ስኬት ቁልፍ ነገር ነው። 

ባል ሚስቱን እግዚአብሔር በፀጋው የሰጠው የሕይወት ባልደረባ አድርጎ ሲመለከታት፥  አመለካከቱ እጅግ ጥልቅ የሆነ ምስጋና፥ ፍቅር፥ እንክብካቤና መሰጠት ይሆናል። በአንጻሩ ደግሞ ተፎካካሪሪውና ተገዳዳሪው ወይም ፍላጎቱንና ጥያቄውን ልታገለግልለት የተቀመጠች አንዲት ሴት አድርጎ የሚያይ ከሆነ፥ አመለካከቱ በትዕቢት፥ በቁጣ የተሞላ ከመሆኑም በላይ ጥላቻን ሳይቀር ማሳደግ ይጀምራል። 

ሚስትም በሙሉ ኃይልዋ እንድታፈቅረው ለእርሱና ለቤተሰቧ ሕይወቷን እንድትሰዋ እግዚአብሔር የሰጣት ስጦታ አድርጋ ባልዋን የምትመለከተው ከሆነ፥ አመለካከቷ የፍቅር፥ የመሰጠት፥ የድጋፍና የመሥዋዕትነት ይሆናል። ነገር ግን ባልዋን የሚጨቁናትና እርሱንና የተቀረውን ቤተሰብ ለማገልገል ያስቀመጣት አድርጋ የምታይ ከሆነ አመለካከቷ በምሬት፥ በእምቢተኝነት የተሞላ ይሆናል ቀስ በቀስም ይህ አመለካከት ወደ ዓመፅ ያድጋል። 

ባልና ሚስት በእርሱ ውስጥ ያለውን ዕቅድ ለማከናወን ፈቃደኞች የሆኑ የእግዚአብሔር ልጆች አድርገው ራሳቸውን የሚቆጥሩ ከሆኑ፥  ወደ እግዚአብሔር የመቅረብን አመለካከት ያዳብራሉ፤ አንዳቸው አንዳቸውን ለመርዳትና ለመቀራረብ እጅግ ይጥራሉ። ሰላምና ደስታ የተሞላበት የእርካታ ሕይወት ለመኖር የሚያስፈልገውን ምግባር ያገኛሉ። 

ሁለቱ ገንዘብንንና ቁሳዊ ሀብትን እጅግ ዋና ነገር አድርገው መመልከት ከጀመሩ አንዳቸው ስለአንዳቸው ስለሌሎች ሰዎችና ስለሚገጥማቸው ሁኔታ የሚኖራቸው አመለካከት በራስ ወዳድነትና በጥላቻ የተሞላ ይሆናል። ነገር ግን የመኖራቸው ምክንያትና በጋብቻ መተሳሰራቸው  ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፍቅሩን ለሰዎች ሁሉ የሚያሳይበት መሣሪያ አድርገው የሚያስቡ ከሆነ፥   በዙሪያቸው ያሉ ሰዎች ጌታን የበለጠ እንዲያውቁ ለማገልገል ፈቃደኛ የመሆን አመለካከት ይኖራቸዋል። ቤታቸውም የጌታ ማረፊያ (ትንሿ) ቤተ ክርስቲያን ትሆናለች። 

በመሆኑም በመጀመሪያ በጋብቻ ሕይወታችሁ በእርግጥኝነት የሚያጋጥማችሁን ብዙ ተግዳድሮት ለመቋቋም፥ ደስታና እርካታ የተመላበት ሕይወት ለመምራት እንድትችሉ የሚረዳችሁን አዲስ አመለካከት ለማዳበር፥ አሳባችሁን፥ ራዕያችሁንና ዋጋ የምትሰጡትን ነገር መመርመር እጅግ አስፈላጊ ነው። 

ሌላው ልናስታውስ የሚገባን « አመለካከት» ከሰው ወደሰው የሚጋባ ነው። በመሆኑም የትዳር ጓደኛችሁ አዎንታዊ ያይደለ ወይም እጅግ አሉታዊ ያይደለ ቢኖራት ወይም ቢኖረው ከልብ በሆነ ጸሎቶቻችሁና በመልክካም በታጋሽነታችሁ እና በደስተኛ አመለካከታችሁ መለወጥ ይኖርባችኋል።  

ነገሮችን በአሉታ የሚመለከት  ወይም የሚትመለከት የትዳር ጓደኛ ቢያጋጥማችሁ አሉታዊ በሆነ መንገድ በመመለሳችሁ የምታሸንፉ አይምሰላችሁ።  በክፉ ስትመልሱ ነገሮችን የተሻለ የምታደርጉበትን እድል ከማጣታችሁ በላይ ዘላቂ ሰላማችሁን በማጣት « ክፉን በመልካም እንጂ በክፉ አታሸንፍ» በማለት ካዘዘ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር የሚኖራችሁን ግንኙነት ታበላሻላችሁ። 


እስከአሁን ካልጀመራችሁ፥ ነገሮች ከእጃችሁ ከመውጣታቸው በፊት ስለ ትዳር ጓደኛችሁና ስለ ሕይወታችሁ ያላችሁን እመለካከት እንድትለውጡ እመክራችኋለሁ። ብዙ ሰዎች እድላቸውን ወርውረው ስለ ትዳር ጓደኛቸው ያላቸውን አመለካከት ለመለወጥ ምንም ጥረት ሳያደርጉ የትዳር ጓደኛቸው ወደ ጌታ ሲሄዱ ወይም ትዳራቸው ወደ አልሆነ አቅጣጫ ሲሄድ በፀፀት እንዳይወሰዱ እፈራለሁ።