Tuesday, July 30, 2013

ጸሎተ ሃይማኖት (አስራ አንደኛ ክፍል)



ስለ እኛ ተሰቀለ፤ ታመመ፤ ሞተ፤ ተቀበረም በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ተለይቶ ተነሣ በቅዱሳት መጻሕፍት እንደተጻፈ፤ በክብር ወደ ሰማይ ዐረገ፤ በአባቱም ቀኝ ተቀመጠ፤ ዳግመኛ ሕያዋንን ሙታንንም ይገዛ ዘንድ በጌትነት ይመጣል፤ ለመንግሥቱም ፍጻሜ የለውም። 

  1. ስለ እኛ ተሰቀለ
አንዳንድ የመስቀሉ ቃል ያልተገለጠላቸው ሰዎች እንዴት ሰው የተገደለበትን መሣሪያ ታገኑታላችሁ ይሉናል። ነገር ግን ይህ የሞት መሣሪያ የሕይወት ምልክት የሆነው በእርሱ ላይ ከተከናወነው ነገር የተነሣ ነው። 
• መስቀሉ መርገም የተሻረበት ነው፤ 
በገነት መካከል ያለው ዛፍ እርግማንን ወደሰዎች ያመጣ ነው። የቀደመው ሰው አዳምና እናታችን ሄዋን አትብሉ የተባሉትን ሲበሉ በመርገም ውስጥ ነበር የወደቁት፤ በመስቀሉ ግን ያ እርግማናችን ነው የተደመሰሰው፤ ቅዱስ ጳውሎስ ስለዚህ ሲናገር «በእንጨት የሚሰቀል ሁሉ የተረገመ ነው ተብሎ ተጽፎአልና ክርስቶስ ስለ እኛ እርግማን ሆኖ ከሕግ እርግማን ዋጀን፤» ይላል። ገላትያ 3፥19። 
• መስቀሉ ጥል የተገደለበት ነው፤ 
አሁንም በገነት መካከል ያለው ዛፍ በሰውና በእግዚአብሔር እንዲሁም በሰውና በሰው መካከልም ከዚያም አልፎ በሰው ሕይወት ውስጥ ጥልን የተከለ ነበር። በሰው ሕይወት ውስጥ ወዲያው የተገለጠው ራቁትነት፥ ፍርሃት፥ ራቁትነት እና ከእግዚአብሔር መሸሽ ነበር። ሰው በእግዚአብሔር ፊት ጥል የሆነውን ነገር ማድረግ ጀመረ፤ ከራሱና ከሌላው አምሳያው ጋር መጣላት ጀመረ፤ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ግን «እርሱ ሰላማችን ነውና፤ ሁለቱን ያዋሐደ በአዋጅ የተነገሩትንም የትእዛዛትን ሕግ ሽሮ በመካከል ያለውን የጥል ግድግዳን በሥጋው ያፈረሰ፤ ይህም ከሁለታቸው አንድን አዲስን ሰው በራሱ ይፈጥር ዘንድ ሰላምንም ያደርግ ዘንድ ጥልንም በመስቀሉ ገድሎ በእርሱ ሁለታቸውን በአንድ አካል ከእግዚአብሔር ጋር ያስታርቅ ዘንድ ነው።» ኤፌሶን 2፥14-16
• መስቀሉ የእርቅ ምልክት ነው። 
የእግዚአብሔር ልጅ ለእኛ ለሰው ልጆች የሰበከልን የእግዚአብሔር መንግሥት የተጠቃለለው በመስቀሉ ላይ ባሳየን የፍቅር መሥዋዕትነት ነው። ከዚህ በፊት በብሉይ ኪዳን ይሠዉ ስለነበሩት መሥዋዕቶች ስንነጋገር እንዳልነው፥ ክርስቶስ በመስቀሉ ላይ ያከናወነልን እርቅ ነው። በመሆኑም መስቀል ሲባል ጌታ የሞተበት ሁኔታ ብቻ ሳይሆን አጠቃላይ ሰውን ከአምላኩ ለማስታረቅ ያከናወነው ድርጊት ነው። በመሆኑም ወንጌል ራሱ የመስቀሉ ቃል ተብሎአል። ሮሜ 1። 18። 
• መስቀሉ የእግዚአብሔር ጥበብ የተገለጠበት ነው። 
በመስቀሉ በኩል ያየነው እግዚአብሔር እጅግ አስደናቂ የሆነ ነው። ወደሰዎች መከራና ሥቃይ የቀረበ። የሰዎችን የልብ ስብራት የዳሰሰ እግዚአብሔር ነው። በትህትናና በዝምታ የመጣ እግዚአብሔር ነው። ክብሩን ሁሉ የተወ እግዚአብሔር ነው። በመሆኑም ልክ ኤልያስ በእግዚአብሔር ተራራ ላይ በእሳት እና በአውሎ ነፋስ እንደፈለገው በዕውቀታቸው ወይም በዚህ ዓለም ከፍታዎች ውስጥ የፈለጉት አላገኙትም። እርሱ የተገኘው በመስቀል ላይ ከወንጀለኞች ጋር፥ በነዘኬዎስ ቤት ከኃጢአተኞች ጋር፥ በጌርጌሶን ከመቃብር አዳሪዎች ጋር፥ በመንገድ ደም ከሚፈሳቸው ጋር፥ በቤት ከታወቁ ኃጢአተኞች ጋር ነው። በዚህም የዓለምን ጥበብ ሁሉ ከንቱ አደረገው። ክብር ለእርሱ ይሁን

  1. ታመመ ( መከራ ተቀበለ) 

የክርስቶስን ሕማም በምናስብበት ወቅት የምናስባቸው የሕማማቱን ሳምንቶች ብቻ አይደለም። የሕማሙ ጉዞ ከልደቱ እስከሞቱ ያለው ሁሉ ነው። ታመመ የሚለው ቃል ጌታ በመከራ ወደ እኛ እንዴት እንደቀረበን የሚያመለክት ነው። ዕብራውያን ስለዚህ ሲናገር እንዲህ ይላል። « ስለዚህ የሕዝብን ኃጢአት ለማስተስረይ፥ ለእግዚአብሔር በሆነው ነገር ሁሉ የሚምርና የታመነ ሊቀ ካህናት እንዲሆን፥ በነገር ሁሉ ወንድሞቹን ሊመስል ተገባው።» በማለት በነገር ሁሉ እኛን እንደመሰለ ይነግረናል። በዚሁ አንቀጽ ላይ እንደገና ዝቅ ብሎ ሲናገር « ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደ እኛ የተፈተነ ነው እንጂ፥ በድካማችን ሊራራልን የማይችል ሊቀ ካህናት የለንም።» ይላል። ዕብራውያን 2፥17፤4፥15። ቅዱስ ጴጥሮስም የእርሱ መከራ ለእኛ መከራ የእርሱ ሕማም ለእኛ ሕማም የመጽናናት ምክንያት እንደሆነ ሲያስተምረን እንዲህ ብሎአል፦ « የተጠራችሁለት ለዚህ ነውና፤ ክርስቶስ ደግሞ ፍለጋውን እንድትከተሉ ምሳሌ ትቶላችሁ ስለ እናንተ መከራን ተቀብሎአልና። እርሱም ኃጢአት አላደረገም፥ ተንኰልም በአፉ አልተገኘበትም፤ሲሰድቡት መልሶ አልተሳደበም መከራንም ሲቀበል አልዛተም፥ ነገር ግን በጽድቅ ለሚፈርደው ራሱን አሳልፎ ሰጠ፤» 1 ጴጥሮስ 2፥21-23 

Tuesday, July 16, 2013

ጸሎተ ሃይማኖት (አሥረኛ ክፍል)

Read in PDF
ባለፈው ክፍል ትምህርታችን ላይ ስለ ሊቀ ካህኑ አገልግሎት የሚመለከቱ ሦስት ዋና ዋና ነገሮች ማለትም መሥዋዕቱን፥ ዕርቅንና ቡራኬን ተመልክተናል። በዚህ ክፍል ላይ እንዳልነው በብሉይ ኪዳን የሚሠዉት  መሥዋዕቶች በሙሉ የሚያመለክቱት ክርስቶስን ነው። ትምህርተ ሃይማኖትና ክርስቲያናዊ ሕይወት ከተባለው የሊቀ ጉባኤ አበራ አበራ መጽሐፍ እጅግ ጠቃሚ የሆኑ ጉዳዮችን በዚህ ርእስ ዙሪያ ያስቀምጣል። በመሆኑም ስለ ክርስቶስ መሥዋዕትነት የሚያትተንውን ምዕራፍ ለጥናታችን እንዲያመች በአርእስት በመከፋፈል እቅርበነዋል። 

1. የኃጢአት አደገኛነት
« ኃጢአት ከእግዚአብሔር መጣላትን መከራና ሞትን እንዳመጣብን ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሰክራሉ። ሆኖም አንዳንድ የሃይማኖት ወገኖች በሰው ሰውኛ አስተሳሰብ እየተመሩ የኃጢአት ሥርየት የለም፥ ከኃጢአታችንም የሚያድነን፥ ከእግዚአብሔርም የሚያስታርቀን አያስፈልግም ብለው ያምናሉ። እንደ እግዚአብሔር ቃል ከሆነ የኃጢአት ሥርየት ከሌለ ማንም ወደ እግዚአብሔር ሊቀርብ ከቶ አይችልም። እውነትኛውም አምልኮ በዚህ ላይ ተመሠረተ ነው። በኦሪት ሕግ የመሥዋዕቱና የቁርባኑ ሥርዓት ሁሉ የሚያስተምረን ስለ ኃጢአት ሥርየት ነው።»

2. ደም ሳይፈስ ሥርየት የለም
« ደምም ሳይፈስ ሥርየት የለም» እንደ ተባለ በኦሪት ሥርዓት መሠረት የእንስሳት ደም በመሠዊያው ላይ እየፈሰሰ የሰዎችን ኃጢአት ሁሉ ለአማናዊው መሥዋዕት ምሳሌ በመሆን ያስተሠርይ ነበር። (ዕብ 9፥6_22፤ ዘሌዋ 17፥11) እውነተኛው የእግዚአብሔር በግ በመሠዊያው ላይ ደሙን እስኪያፈስ ድረስ በኦሪቱ የፈሰሰው የእንስሳት ደም ሁሉ ምሳሌና ትንቢት ነበር። የእግዚአብሔር በግ ክርስቶስ የሰዎችን ልጆች ሁሉ ኃጢአት ለማስተሥረይ በመስቀል መሠዊያ ላይ ደሙን አፍስሶ የኃጢአት ሥርየትን አስገኝቶልና።

3. በመሥዋዕቱ የሚገኘው እርቅ
« እንግዲህ ሰዎች ፍጹም ቅዱስ ከሆነው እግዚአብሔር ጋር ሊታረቁና ሊቀርቡ የሚችሉት በክርስቶስ መሥዋዕትነት ባገኙት የኃጢአት ሥርየት ነው።«  ኃጢአተኞችን ሊያድን ክርስቶስ ኢየሱስ ወደ ዓለም መጣ የሚለው ቃል የታመነና ሁሉ እንዲቀበሉት የተገባ ነው። » በማለት ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ያስገነዝበናል። . . . እንግዲህ በሰዎችና በእግዚአብሔር መካከል አንድ መካከለኛ ሆኖ ክርስቶስ እንዳስታረቀን ማመን አለብን፤ ያለ እርሱ . . . ማንም ወደቅዱስና ፍጹም አምላክ ሊደርስ አይችልም። አንዳንድ የሃይማኖት ወገኖች ወገኖች ወይም የፍልስፍና ሰዎች የሚሉትን በመከተል ማንም  ሰው ብቻዬን ወደ እግዚአብሔር እደርሳለሁ ቢል እርሱ ገና የሃይማኖትን ነአር አላወቀም፤ የኃያል አምላክን መልዕልተ ባሕርይ ገና አልተረዳም። « ሰዎች ሁሉ ሊድኑና እውነቱን ወደ ማወቅ ሊደርሱ በሚወድ በእግዚአብሔር በመድኃኒታችን ፊት መልካምና ደስ የሚያሰኝ ይህ ነው፤ ካለ በኋላ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በመቀጠል፦ አንድ እግዚአብሔር አለና፥ በእግዚአብሔርና በሰው መካከል ያለው መካከለኛው ደግሞ አንድ ነው፥ እርሱም ሰው የሆነ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው። ራሱንም ለሁሉ ቤዛ ሰጠ» ብሏል። ( 1ኛ ጢሞቴዎስ 2፥3_6) መካከለኛ መሆን ወይም አስታራቂነት በክርስቶስ የማዳን ሥራና ቤዛነት ላይ የተመሠረተ ነገር እንደ ሆነ ከሐዋርያው ቃል ለመረዳት እንችላለን። »

4. በመሥዋዕቱ የተከፈተው መንገድ
« በወንጌል ያለ ክርስቶስ ወደ እግዚአብሔር የሚቀርብ እንደ ሌለ ተጽፏል። እርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚያደርስ እውነተኛ መንገድና በር ነው። ያለ እርሱ መንገዱም በሩም በኃጢአት ግርግዳ የተዘጋ ነው። በእርሱ ባገኘነው የኃጢአት ሥርየት የጥሉ ግርግዳ ስለፈረሰ ወደ ወደ እግዚአብሔር የሚያገናኘው መንገድ ተከፍቶአል። እርሱ ራሱ መንገድም፥ እውነትም፥ ሕይወትም፥ ነውና በእርሱ በኩል ካልሆነ ወደ አብ የሚመጣ የለም ። (ዮሐንስ 14፥6) በእርሱ ሥጋዌ (ሰው መሆን ) በማመን እርሱ በከፈተው የጽድቅ መንገድ፥ እርሱ በመስቀሉ ባስገነው ቤዛ ካልሆነ በቀር በገሐድ በሥጋዌ (ሰው በመሆን) ያልተገለጠውን አብን የሚያገኘው የለም ማለት ነው። (ዮሐንስ 14፥6 ትርጓሜውን ተመልከት፤

5. በደሙ የተመረቀልን መንገድ
ወደ እግዚአብሔር የሚያደርሰን አማናዊው መንገድ (ፍኖተ ጽድቅ ወሕይወት) የተባለው የክርስቶስ ሥጋና ደም ነው። እግዚአብሔር ወደ አለበት ወደ ቅድስት ለመግባት የምንችለው በክርስቶስ ሥጋ በኩል አንደሆነ ቅዱስ ጳውሎስ ለዕብራውን ክርስቲያኖች ሲጽፍ፦ እንግዲህ ወንድሞች ሆይ በመረቀልን በአዲስና በሕያው መንገድ ወደ ቅድስት በኢየሱስ ደም በመጋረጃው ማለት በሥጋው በኩል እንድንገባ ድፍረት እንዳለንና እንዲሁም « በእግዚአብሔር ቤት ላይ የሆነ ታላቅ ካህን » እንዳለን ገልጾናል። « ወደ ቅድስት በኢየሱስ ደም በመጋረጃው ማለት በሥጋው በኩል እንድንገባ ድፍረት ስላለን» የሚለውን የሐዋርያውን ቃል ትርጉም ወይም ምሥጢር የምንገነዘበው ሰው በሠራው በደልና ኃጢአት ምክንያት ከእግዚአብሔር ተለይቶ በፍርሃትና በጭንቀት ሲኖር ሳለ ክርስቶስ ሰው ሆኖ ደሙን አፍስሶ ኃጢአቱን አስወግዶ ከራሱ ጋር አስታርቆ « ወደ ቅድስት የሚወስደውን መንገድ»  እንዲከፈት አድርጐ ወደ ሰማያዊው መቅደስ ወደ ጸጋው ዙፋን ወደ እግዚአብሔር ለመምጣት ለመግባት መብትን « ድፍረትን እንዲሁም የጸጋ ልጅነትን እንዲያገኝ ሥልጣንን እንደሰጠው በማመን ነው። (ዕብራውያን 10፥19-22፤ 9፥8-28፤ 4፥16፤ ዮሐንስ 1፥12) የቀድሞው የብሉይ ኪዳን መንገድ ወይም ሥርዓት የሰውን ኃጢአት ስለ ማያስወግድ ከእግዚአብሔር ስለ ማያስታርቅ እግዚአብሔር በፈቀደውና በወደደው « በአዲስና በሕያው መንገድ» ወደ እርሱ እንድንመጣ አድርጎናል። ይኸውም መንገድ በኦሪቱ ሊቀ ካህናትነት እንደሆነ ሐዋርያው ለዕብራውያን በጻፈው መልእክቱ አረጋግጦልናል። እንግዲህ ወደ ቅድስት የሚወስደው መንገድ ወደ እግዚአብሔር የሚያደርሰው መንገድ በኦሪቱ  ሥርዓት በቤተ መቅደሱ መጋረጃ ተዘግቶ የነበረውን በዕለተ ዓርብ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ሆኖ በሥጋው በፈጸመው መሥዋዕትነትና አስታራቂነት አስወግዶታል። ያን ጊዜ መጋረጃው ተቀዷል (ማቴዎስ 27፥51) በክርስቶስ ለሚያምኑት ሁሉ ወደ ፈጣሪያቸው የሚያደርሱበት የእርቅና የሰላም የጽድቅና የሕይወት መንገድ ተከፍቶላቸዋል።»

6. የአዲስ ኪዳን አስታራቂ
« በመሠረቱ ሰው ወደ እግዚአብሔር መቅረብ የሚቻለው ሰው በሆነው በክርስቶስ በኩል ነው። ከዚያ በፊት ግን ሰው መጀመሪያ ወደ ክርስቶስ ለመቅረብና እርሱን ለማመን የሚቻለው የእግዚአብሔር ረድኤት፥ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ወደ ክርስቶስ ሲስበው ነው። በመሆኑም ክርስቶስ፦ የላከኝ አባቴ በሀብት ስቦ በረድኤት አቅርቦ ካልሰጠኝ በኔ ማመን የሚቻለው የለም ብሏል ( ዮሐንስ 6፥44) እንግዲህ ራሱ እግዚአብሔር እኛ ሰዎችን ኃጢአተኞችን ከራሱ ጋር ለማስታረቅና ለማቅረብ ያሰበውና ያዘጋጀው የጽድቅ መንገድ፥ የሕይወት መንገድ በልጁ ሰው መሆን ማለት በምሥጢረ ሥጋዌና በነገረ መስቀል እንደተገለጸው ተፈጽሟል።  በሥጋዌ፥ ወልደ እግዚአብሔር ክርስቶስ የሰውን ባሕርይ ባሕርዩ በማድረጉ ያን ጊዜ ባሕርያችንን ከእግዚአብሔር ጋር አስታርቋል። ስለዚህ ነው <« የአብ ሊቀ ካህናት የሚሆን እርሱ የሰውን ባሕርይ ከእግዚአብሔር ጋር አስታረቀ» እያልን በሐዋርያት አመክንዮ እምነታችንን የምንገልጸው ። (ሥርዓተ ቅዳሴ፤ ቍጥር 43 ተመልከት)  በመስቀሉ ደግሞ ነፍሱን ስለ ሁላችን ቤዛ አድርጎ በመስጠቱ ሰውን ከእግዚአብሔር አጣልቶና አርቆት የነበረውን ኃጢአትን አስወግዶ እርቅና ሰላምን አስገኝቶልናል። ክርስቶስ ስለ ኃጢአታችን መሥዋዕት በመሆኑ እውነተኛ አስታራቂአችን ሆኗል። ቤተ ክርስቲያንም በእርሱ ስም በእርሱ መሥዋዕት የማስታረቁን ሥራ እርሱ ዳግመኛ እስኪመጣ ድረስ በኃላፊነት እንድትሠራ ታዛለች። (2 ቆሮንቶስ 5፥18-21፤ 1 ቆሮንቶስ 11፥23-26፤ ማቴዎስ 28፥19-20)

7.  እንደመልከ ጼዴቅ ባለ ክህነት የዘለዓለም ካህን የሆነ
« እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ሹመት የዓለም ካህን እንደሆንክ» የተባለለት « እርሱ. . . ለዘለዓለም ይኖራል ክህነቱ አይሻርምና። ዘወትር በእሱ በኩል ወደ እግዚአብሔር የሚቀርቡትን ሊያድናቸው ይቻለዋል፤ ለዘለዓለም ሕያው ነውና ያስታርቃቸዋል። እንዲህ ያለ የካህናት አለቃ ይገባናል. . . ከሰማያት በላይ የሆነ . . . ኦሪትስ የሚሞት ሰውን ሊቀ ካህናት አድርጋ ትሾማለች፤ ከኦሪት በኋላ የመጣው የእግዚአብሔር የመሐላ ቃሉ ግን ዘለዓለም የማይለወጥ ፍጹም ወልድን ካህን አድርጎ ሾመልን። ( ዕብራውያን 7፥20-28)  ክርስቶስ መካከለኛ የተባለበት አዳምና ልጆቹ ሁሉ በኃጢአት ምክንያት ከእግዚአብሔር ጋር ተጣልተው፥ ተለይተውና ርቀው የነበሩን በማስታረቁና በማቅረቡ ነው። « ለወንጌል ሊቀ ካህናት ለመንግሥተ ሰማት አስታራቂ ሆነ . . . በከበረ ደሙ ፈሳሽነት በዓለመ ሥጋ በዓለመ ነፍስ ያሉትን አዳናቸው አነጻቸው ወደ ቅዱስ እግዚአብሔር አቀረባቸው፤ ዕብራውያን 12፥24  በቅድሚያ እርሱ ራሱ በሥጋ ተዛምዶ ማለትም ሰው በመሆኑ ወደ እኛ ቀርቧል፤ ከእኛም ጋር ታርቋል። እንግዲህ እርሱ ራሱ በሰውነቱ ቀርቦ አቅርቦናል፤ ታርቆ አስታርቆናል።







Tuesday, July 9, 2013

ጸሎተ ሃይማኖት (ዘጠነኛ ክፍል)

 Read in PDF

ኮነ ብእሴ ወተሰቅለ በእንቲአነ በመዋዕለ ጲላጦስ ጰንጤናዊ። ሐመ ወሞተ ወተቀብረ ወተንሥአ እሙታን አመ ሣልስት ዕለት በከመ ጽሑፍ ውስተ ቅዱሳት መጻሕፍት። ዐርገ በስብሐት ውስተ ሰማያት ወነበረ በየማነ አቡሁ። ዳግመ ይመጽእ በስብሐት ይኰንን ሕያዋነ ወሙታነ። ወአልቦ ማኅለቅት ለመንግሥቱ።  

ሰው ሁኖ በጰንጤናዊው በጲላጦስ ዘመን ስለ እኛ ተሰቀለ። ታመመ፥ ሞተ ተቀበረም በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፤ በቅዱሳት መጻሕፍት እንደተጻፈ። በክብር ወደ ሰማይ ዐረገ በአባቱም አኝ ተቀመጠ። ዳግመኛ ሕያዋንን ሙታንንም ይገዛ ዘንድ በጌትነት ይመጣል። ለመንግሥቱም ፍጻሜ የለውም። 

1 . ሰው ሁኖ. . . 
የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን በዚህ ምድር መመላለስ በምናሰላስልበት ወቅት ልንዘነጋው የማይገባን ነገር ቢኖር እርሱ በዚህ ምድር የተመላለሰው ፍጹም ሰው ሆኖ ነው። አንዳንድ ሰዎች አምላክነቱን ያገነኑ መስሎአቸው ሰውነቱን ለማሳነስ ይሞክራሉ። ይህን የጸሎተ ሃይማኖት የጥናት ጉዞአችንን ስንጀምር እንዳልነው በክርስትና ትምህርት ላይ በተለይም በነገረ ክርስቶስ (ምሥጢረ ሥጋዌ) እውነት ላይ ከሚነሱት የስህተት ትምህርቶች አንዱ የኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም ሰውነት መካድ ነው። እነዚህም ስሕተቶች ሦስት ዓይነቶች ናቸው፤ አንደኛው « ሥጋውን ከሰማይ ይዞ ወረደ የሚል ነው። ሁለተኛው « ሰው መስሎ ተመላለሰ» የሚል ነው። ሦስተኛው « ሰውነቱን አምላክነቱ ውጦታል» የሚል ነው። ቤተ ክርስቲያን እነዚህን ስህተቶች ፈጽሞ አልተቀበለችውም። ወንጌላውያኑ እንደዘገቡትና ሐዋርያት እንደአስተማሩን ኦርቶዶክሳውያን አባቶቻችንም « ሰው ሆነ» ማለት ብቻ ሳይሆን ይህ ሰው የሆነው ጌታ « የአብርሃም ልጅ» « የዳዊት ልጅ» እንደሆነ መስክረዋል፤ ሐረገ ትውልዱንም ቆጥረዋል። ማቴዎስ 1፥1።  የተዋሃደው የማንን ሥጋ እንደሆነ ቅዱስ መጽሐፍ ሲናገር « የአብርሃምን ዘር ይዞአል እንጂ የያዘው የመላእክትን አይደለም »  ይላል። ዕብራውያን 2፥16።  ስለ ክርስቶስ ፍጹም ሰውነት  መጽሐፍ ቅዱሳችንንን ስናጠና የሚከተሉትን የመጽሐፍ ቅዱስ እውነቶችን እናገኛለን። 
• ከአብርሃም ዘር ከሆነችው ከድንግል የተወለደ፤ ( ማቴዎስ 1፥1 ገላትያ 4፥4) 
• በየጥቂቱ ያደገ ( ሉቃስ 2፥52፤ 4፥16) 
• ሕግን ሁሉ ፈጸመ፤ (ሉቃስ 2፥27፤ ገላትያ4፥4) 
• ተራበ ማቴዎስ 4፥2፤ 21፥18። 
• ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደእኛ ተፈተነ (ዕብራውያን 4፥15) 

2. በጰንጤናዊው ጲላጦስ ዘመን 
ይህ ቁልፍ የሆነ ቃል ነው። በተለይ በዚህ ዘመን፥ ዘመናውያን ምሑራን በ«ታሪካዊው ኢየሱስ» እና « በቤተ ክርስቲያን ኢየሱስ» ማለትም በታሪክ በምናገኘው ኢየሱስ እና ቤተ ክርስቲያን በምትሰብከው ኢየሱስ መካከል ልዩነት እንዳለ በሚሰብኩበት ወቅት፥ የኒው ኤጅ ምሑራን እኛ ሁላችን ኢየሱስ እንደሆን በውስጣችንም ክርስቶስነት እንዳለን በሚነግሩን ወቅት የምናመልከው ጌታ ኢየሱስ ማን እንደሆነ ማወቅ አለብን። የምናመልከው የምንሰግድለት ኢየሱስ በታሪክ የተገለጠውን ኢየሱስ ነው። የአባቶቻችንን ቋንቋ ለመጠቀም የምናመልከው ኢየሱስ « ትንቢት የተነገረለት ሱባኤ የተቆጠረለት ነው።» ወንጌላውያኑ እንደመሰከሩትም (ማቴዎስ 27፥2፤ ሉቃስ 3፥1፤ ሐዋርያቱም እንዳስተማሩት ሐዋ ሥራ 4፥27፤ 1 ጢሞቴዎስ 6፥13) ጌታ በጴንጤናዊው በጲላጦስ ዘመን ስለ እኛ ተሰቀለ።

3. ስለ እኛ ተሰቀለ
እኛን ለማዳን ሲል በሚለው ትምህርታችን ላይ እንደተመለከትነው፥ ጌታ እኛን የሚያድነን ለምን እንደሆነ ተመልክተናል፤ በኃጢአት ስንወድቅ ሁለት ዋና ነገሮች ተከናውኖአል። የእግዚአብሔር ክብር ጎድሎናል። እግዚአብሔር ካዘጋጀልን መንገድ ወጥተን አቅጣጫ ስተናል። (ኃጢአት ማለት መጉደልና አቅጣጫ መሳትም የሆነውም ለዚህ ነው። ) እግዚአብሔር ለእኛ ያዘጋጀልንን ሕይወት ለመኖር ስላልቻልን፥ የእግዚአብሔር ልጅ ከወደቅንበት የኃጢአት አረንቋ ሊያወጣን፥ ሊያድነንና ወደ አባቱ መንግሥት ሊያፈልሰን ወደደ። ይህ ደግሞ የሆነው በመስቀሉ ነው። እዚህ ላይ ልንጠይቀው የሚገባን ነገር ቢኖር መስቀሉ ወይም የመስቀል ሞት ለምን አስፈለገ የሚል ነው። መልሱን የምንገልጠው ጌታ በሥጋዌው ሊያከናውናቸው ከመጣባቸው አገልግሎቶች አንዱ የሆነውን የሊቀ ካህንነቱን ሥራ በመተንተን ነው።
ሊቀ ካህኑ በአገልግሎቱ ውስጥ ሦስት ዋና ዋና ነገሮች አሉት። መሥዋዕት፥ ዕርቅ እና ቡራኬ ናቸው።

Tuesday, July 2, 2013

ጸሎተ ሃይማኖት (ስምንተኛ ክፍል)

Read in PDF
ተሰብአ ወተሠገወ እመንፈስ ቅዱስ ወእማርያም እምቅድስት ድንግል።

ከመንፈስ ቅዱስ የተነሣ ከቅድስት ድንግል ማርያም ፈጽሞ ሰው ሆነ


መግቢያ

ባለፈው ክፍላችን ስለ እግዚአብሔር ወልድ ስለ ሐልዎቱ ቅድመ ዓለም ስለነበረው አነዋወሩ አባቶች ያስቀመጡትን ሀረግ አይተናል። በዚህ ክፍላችን ደግሞ በባሕርያችን መመኪያ በቅድስት ድንግል ማርያም የተከናወነወነውን አስደናቂ ሥራ እናያለን።

ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም ስናነሣ፥ ኦርቶዶክሳውያን መምህራን ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም ክብር ለማሰላሰል ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም ማንነት ለመጻፍ፥ ለማስተማር መነሻ ያደረጉት ምንድነው የሚል ነው?  ለማንኛውም መንፈሳዊ እውነት መነሻችን የእግዚአብሔር ቃል እንደመሆኑ መጠን ኦርቶዶክሳውያን መምህራን መነሻ ያደረጉት መጻሕፍት አምላካውያት የአምላክ መጻሕፍት ብለው የሚጠሩዋቸውን ቅዱሳት መጻሕፍትን መነሻ አድርገው ነው። ይህ ወደሚቀጥለው ጥያቄ ይመራናል። ቅዱሳት መጻሕፍትን የተገነዘቡት ወይም ያነበቡት እንዴት ነው? መረጃ እንዳለበት መጽሐፍ በማየት ኢንፎርሜሽን ነው የሰበሰቡት ወይስ የእግዚአብሔር ቃል የአምላክን ልጅ በሥጋ መገለጥ የሚያውጅ መጽሐፍ መሆኑን በመመልከት የመሲሑን መምጣት እና ለመምጣቱ ምን ዓይነት ዝግጅት እንደነበረው በመመርመር ነው? የዚህ ጥያቄ አመላለሳችን ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም የሚኖረንን አመለካከት በብዙ መንገድ የሚወስነው ይሆናል?

መጽሐፍ ቅዱስን እንደ መረጃ መጽሐፍ ብቻ የምንመለከት ከሆነ  በዚህ በአገረ አሜሪካ የታወቀ የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት እንዳለው « ስለዚህች ማርያም መጽሐፍ ቅዱስ ብዙም አይናገርም» በማለት ታላቁን የእግዚአብሔር የማዳን ታሪክ እንደቀልድ እናልፈዋለን። ነገር ግን እንደኦርቶዶክሳውያን አባቶች መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጅ በሥጋ ስለመገለጡ የሚናገር መጽሐፍ ከሆነ ስለቅድስት ድንግል ማርያም እግዚአብሔር በቃሉ የሚናገረውን ከዘፍጥረት መጽሐፍ ከመጀመሪያዎቹ ምዕራፎች ጀምሮ እስከ ራዕየ ዮሐንስ እናያለን። በመረጃነት የተጻፈውን ከሆነ የምንፈልገው 90% የሆነውን የምናገኘው ከሉቃስ ወንጌል ነው። ሆኖም ግን መነሻችን እግዚአብሔር ወልድ በሥጋ መገለጡ ከሆነ ግን ከአዳም እንጀምራለን። ለዚህም ነው አባቶች በብሉይ ኪዳን የእግዚአብሔር ታሪክ ውስጥ ክርስቶስን በምሳሌ እንዳገኙት ሁሉ እርሱ የተገለጠባትን ከእርሷ የተወለደባትን ቅድስት ድንግል ማርያምንም በምሳሌ ያገኙት።  በዚህ ተመስርተው አባቶች ቅድስት ድንግል ማርያምን ከብሉይ ኪዳን ቅዱሳንና በእነርሱ ሕይወት ካደረገው ድንቅ ነገር ጋር አስተያይተው ተናግረዋል። ዳግማዊት ሔዋን ብለዋታል። (ዘፍጥረት 3)  የያዕቆብ መሰላል ( ዘፍጥረት 28፥12 ብለዋታል፤  የሙሴ ጽላት ብለዋታል።  የአሮን በትር ብለዋታል። ። . . .

ስለ ክብረ ቅድስት ድንግል ማርያም የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ የነበሩት ፖፕ ሸኑዳ የጻፉትን መመልከቱ ጠቃሚ ስለሆነ በከፊል በዚህ ክፍል ላይ በከፊል ተርጉመን አቅርበነዋል።


« ስለ ድንግል ማርያም ክብር፥ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመዘገበውን የድንግልን ቃል መጥቀስ ብቻ በቂ ነው፦« ከዛሬ ጀምሮ ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ይሉኛል።» ሉቃስ 1፥48። « ትውልድ ሁሉ» የሚለው ሐረግ ድንግል ማርያምን ማክበር ለሁሉም የተሰጠ ዶግማ መሆኑና፥ በክርስቶስ ሰው መሆን ተጀምሮ እስከ ዓለም ፍጻሜ የሚቀጥል መሆኑን የሚያመለክት ነው። ለድንግል ማርያም የተሰጡ ክብሮች በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ  ተመዝግበዋል። ለምሳሌ ከቅድስት ማርያም እናት ጋር በዕድሜ እኩያ የሆነችው ኤልሳቤጥ « የጌታዬ እናት ወደ እኔ ትመጣ ዘንድ እንዴት ይሆንልኛል? እነሆ የሰላምታሽን ድምፅ በጆሮዬ በመጣ ጊዜ ፅንሱ በማኅፀኔ በደስታ ዘሎአልና።» ብላለች። ሉቃስ 1፥43-44) በዚህ ቦታ ላይ ስለ ድንግል ክብር ሊያስደንቀን የሚገባው ነገር ቢኖር የእርሷን ሰላምታ ኤልሳቤጥ ስትሰማ « በመንፈስ ቅዱስ መሞላቷ ነው። (ሉቃስ 1፥41። የድንግልን ድምጽ መስማቷ ብቻ ኤልሳቤጥ በመንፈስ ቅዱስ እንድትሞላ አድርጓታል።

ድንግል ክብርን የተቀበለችው ከሰው ዘር ብቻ አይደለም። ከመላእክትም ተቀብላለች። ይህም ከመልአኩ ከገብርኤል ሰላምታ ግልጥ ነው። « ጸጋን የተመላሽ ሆይ ደስ ይበልሽ። ጌታ ካንቺ ጋር ነው። አንቺ ከሴቶች መካከል የተባረክሽ ነሽ» ነበር ያላት። ሉቃስ 1፥28። « አንቺ ከሴቶች መካከል የተባረክሽ ነሽ » የሚለው ቃል ኤልሳቤጥ ለድንግል ማርያም በሰጠችው ሰላምታ ተደግሞአል። ሊቀ መላእክት ገብርኤል ድንግል ማርያምን ሲያናግር የተጠቀመው ንግግር ካህኑ ዘካርያስን ካናገረበት ንግግር ይልቅ  ታላቅ ክብር ያለው ንግግር ነበር። ሉቃስ 1፥13።. . .

ቅድስት ድንግል ማርያም የትውልድ ሁሉ ምኞት ናት። « የእባቡን ራስ የቀጠቀጠው» ከእርሷ የተገኘው ነው። በዚህም እግዚአብሔር ሰውን ለማዳን የገባው ተስፋ ተፈጽሞአል። ዘፍጥረት 3፥15።

ድንግል የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ እናት እንደመሆኗ ለክርስቶስ የተሰጡት ማዕረጋት ሁሉ ለእርሷ እናትነትም ይሰጣሉ። ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ እውነተኛ ብርሃን ነው። (ዮሐንስ 1፥9) እርሱ ራሱ « እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ» ብሎአል። ዮሐንስ 8፥12። ስለሆነም እናቱ ድንግልም የብርሃን እናት ወይም የእውነተኛው ብርሃን እናት ናት። ክርስቶስ ቅዱሱ እንደሆነ ሁሉ (ሉቃስ 1፥35) ድንግልም የቅዱሱ እናት ናት። ለእረኞች « ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋልና» ተብሎ እንደተነገረ (ሉቃስ 2፥11)እንዲሁ   « ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ያድናቸዋልና» ( ማቴዎስ 1፥21) ስሙ ኢየሱስ ይኸውም አዳኝ እንደተባለ ሁሉ ድንግልም የመድኃኒታችን እናት ናት። ክርስቶስ እግዚአብሔር እንደመሆኑ (ዮሐንስ 1፥1፤ ሮሜ 9፥5) ዮሐንስ 20፥28) ድንግልም የእግዚአብሔር እናት ናት። ክርስቶስ ጌታ እንደሆነ፥ በኤልሳቤጥ ቃል መሠረት ድንግል ማርያም « የጌታዬ እናት ናት» ተብላ ስለተጠራች (ሉቃስ 1፥43) ድንግል የጌታ እናት ናንት። በተመሳሳይ መንገድ እርሷ የአማኑኤል እናት ናት። ማቴዎስ 1፥24። የሥግው ቃል እናት ናት። ዮሐንስ 1፥14።

ቅድስት ድንግል ማርያም የክርስቶስ እናት ከሆነች ያለምንም ጥያቄ የክርስቲያኖች ሁሉ መንፈሳዊ እናት ናት። ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ሳለ ይወደው ለነበረው ሐዋርያ ለቅዱስ ዮሐንስ « እነሆ እናት» ብሎ የተናገረው በቂ ነው። (ዮሐንስ19፥27  ለእኛ « ልጆቼ » በማለት ለጻፈልን ለቅዱስ ዮሐንስ እናት ከሆነች (2 ዮሐንስ 1፥1) ለእኛም ለሁላችን እናት ናት። . . .

ድንግልን የሚያከብር ክርስቶስን ራሱን ያከብራል። እናትን ማክብር ተስፋ ያለው የመጀመሪያ ትእዛዝ ከሆነ (ኤፌሶን 6፥1፤ ዘፀዓት 20፥12) የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን እናትና የሐዋርያትን እናት ድንግል ማክበር አይገባንምን? መልአኩ « መንፈስ ቅዱስ በአንቺ ላይ የመጣል፤ የልዑል ኃይል ይጸልልሻል፤ ስለዚህ ደግሞ ከአንቺ የሚወለደው ቅዱሱ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል » ብሎአት ነበር። (ሉቃስ 1፥35) በኤልሳቤጥ የተመሰገነች እርሷ ነች። ኤልሳቤጥ « ከጌታ የተነገረላት ቃል ይፈጸማልና ያመነች ብፅዕት ናት» ነበር ያለቻት።   ሉቃስ 1፥45።

« ከሴቶች መካከል የተባረክሽ ነሽ» የሚለው ቃል በቅዱስ ገብርኤል እና በቅድስት ኤልሳቤጥ ሲነገር፥ ድንግል በመላው ዓለም ከሚገኙት ሴቶች መካከል የተባረከች ሆና መገኘቷን የሚያመለክት ነው። ምክንያቱም በአካላዊ ቃል ሰው መሆን እርሷ የተቀበለችውን መለኮታዊ ክብር የተቀበሉ ሴቶች ስለሌሉ ነው። እግዚአብሔር ድንግል እመቤታችንን የመረጠው እርሷ ያላትን የቅድስና ባሕርይ ያሟሉ ሌሎች ሴቶች ስለሌሉ ነው። ይህም የእርሷን ከፍታ የሚያመለክት ነው። . . .

እግዚአብሔር በእርሷ ውስጥ በማደሩ ቤተ ክርስቲያን እርሷን ዳግማዊት ሰማይ፥ የመገናኛ ድንኳን፥ የሙሴ ድንኳን ብላ ትጠራለች።

ቤተ ክርስቲያን ድንግልን የእግዚአብሔር ከተማ ወይም ጽዮን ብላ ትጠራታለች፤ ምክንያቱም በመዝሙረ ዳዊት « እግዚአብሔር ጽዮንን መርጦአታልና፤ ማደሪያውም ትሆነው ዘንድ ወድዶአታልና፤ እንዲህ ብሎ፦ ይህች ለዘላለም ማረፊያዬ ና መርጫታለሁና በዚህች አድራለሁ።» መዝሙር 131፥13

ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማይ የወረደ ሕብስት እንደሆነ በመናገር በመና ራሱን በመመሰሉ፥ ( ዮሐንስ 6፥58) ቤተ ክርስቲያን ድንግልን የመና ሙዳይ ትላታለች።

በድንግልና አምላክን ስለመውለዷም ቤተ ክርስቲያን አሁንም ድንግልን የአሮን በትር ትላታለች። ( ዘኍልቍ 17፥8-11።
የምስክሩ ታቦትም የድንግል ማርያም ምሳሌ ነው። ምክንያቱም ታቦቱ በውጭም በውስጥም በወርቅ የተለበጠ ነው። ይህም የእርሷን ንጽሕና ክብር የሚያመለክት ነው። ሁለተኛ ታቦቱ ከማይነቅዝ እንጨት የተሠራ ነው።  ይህም ቅድስናዋን የሚያመለክት ነው። ሦስተኛው  ታቦቱ መናውን የያዘ ነው። ይህም መና ከሰማይ የወረደውን የሕይወት ሕብስት ክርስቶስን የሚያመለክት ነው። በመጨረሻም ታቦቱ የእግዚአብሔር ቃል ክርስቶስን የሚያመለክቱትን  ሁለቱን የሕግ ጽላቶች የያዘ ነው። ዮሐንስ 1፥1።

ያዕቆብ በሕልሙ ያየው ከምድር እስከሰማይ የደረሰው መሰላል የድንግል ማርያም ምሳሌ ነው። ሰማይና ምድር በክርስቶስ ሰው መሆን ተጋጥሞአል። እርሷ ሰማይ ያደረባት ምድር ሆናለች። እርሷ በምድር ሆና ሰማይን በውስጧ ተሸክማለችና፤ (ዘፍጥረት 28፥12።)

ሙሴ የተመለከተው እሳቱ ያላቃጠለው ሐመልማል የድንግል ማርያም ምሳሌ ነው። መንፈስ ቅዱስ በመለኮታዊ እሳትነቱ በእርሷ ላይ ሲመጣ አላቃጠላትምና።

የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የመለኮትና የሰውነት ተዋህዶ ፍሕሙንና እሳቱን እንደሚመስል ሁሉ ቅድስት ድንግል ማርያምም ያን ተዋህዶ የተሸከመች እንደመሆኑዋ፥ በማእጠንት ትመሰላለች። በመሆኑም የአሮን ማዕጠንት ወይም ክብሩዋን ለማጉላት የወርቅ ማዕጠንት ተብላ ትጠራለች።. . .