Monday, March 11, 2013

ጸሎተ ስምዖን ዓምዳዊ (ክፍል 10)


ምዕራፍ ፳፰፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥የመንፈሳዊ መነቃቃትን እሳት ስጠኝ። 
ምዕራፍ ፳፱፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ስለአንተ አብ አሰምቶ የተናገረ፥ እንዲህም ያለ፥ በእርሱ ደስ የተሰኘኹበት የምወደው ልጄ ይህ ነው። አቤቱ እለምንሃለሁ የድምጽህ ቃል ወደ ጆሮዬ ይግባ፥ ነፍሴንም ያድነው፤ የቃልህን ድምጽ የሚሰማ ይድናልና። የሚያይህም እንዲሁ ይድናልና። መዓዛህን የሚያሸት ይድናል። አንተ ሞት የማያገኘው ሕይወት ነህና። 
ምዕራፍ ፴፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል በላይህ ላይ የወረደ፥ ሕያውና ቅዱስ የሆነውን መንፈስህን በእኔ ላይ አሳድር። ወደ መሠወሪያህ ይበር ዘንድ፥ በታላቁ ምጽአትህም ይቀበልህ፥ ዝም በማይል አንደበት አንተን እያመሰገኑ ካሉት አእላፋት ከሚሆኑ አላፋት መላእክት ጋር ጋር አንተን ያመሰግንና ይሰግድልህ ዘንድ ለልቤ መንፈሳዊ ክንፍን ስጠው። 
ምዕራፍ ፴፩፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ እሳትን ልጥል መጣሁ እንድትነድም እወዳለሁ ያልህ፤ በተሐድሶ አዲስ እስክታደርጋት፥ ከሐሳባት እስክትለያት ድረስ በሕሊናዬ ውስጥ እሳትህን አንድድ። በጨለማ ያሉትን ብርሃን፥ ርኵሳንን ቅዱሳን ልታደርጋቸው ያችን እሳት ከጥምቀት ውኃ ጋር ደመርካት፤ይህችም እሳት የኃጢአትን ሸለፈት (ቍልፈት) ከሰዎች የምትገዝር፥ ያረጁ ልማዶችን የምትቆርጥ ከመለኮት ዘንድ የሆነች እዲስ ልብን የምትሰጥ የመንፈስ ቅዱስ ሰይፍ ናት። . . . 

Thursday, March 7, 2013

የእስክንድርያ ትምህርት ቤት (ክፍል አምስት )

 የእስንድርያ ነገረ መለኮት ባህርያት (ካለፈው የቀጠለ። )


ክርስቶስ ሁሉ በሁሉ የሆነበት አሐዳዊ ሕይወት ( ONENESS OF LIFE) 


የእስክንድርያ ትምህርት ቤት ለእኛ ያስተላለፉልን ዋና ነገር ቢኖር በአንዱ በክርስቶስ ያለውን ሕይወት ነው። ርዕሰ መምህሩም ሆነ ተማሪዎቹ የሃይማኖት፥ የፍልስፍናና እና የሳይንስ ጥናታቸውን ከቤተ ክርስቲያናቸው ሕይወት ወይም ከየዕለቱ ኑሮአቸው ነጥለው አያዩትም ነበር። በአንዱ በክርስቶስ ሕይወትነት ያምኑ ነበር። ይህም በጥናታቸው፥ በአምልኮአቸው፥ በአኗኗራቸው፥ በስብከታቸውና በምስክርነታቸው የተገለጠ ነበር።

አርጌንስ ስለ ክርስትና ሕይወት የነበረውን እይታ ሮውን ኤ ግሪር ጠቅለል አድርጎ ሲያቀርበው « የክርስቲያን ሕይወት የመለኮታዊ አስተርእዮ divine revelation) ምላሽ ነው። እግዚአብሔርን በማወቅ እንጀምርና ከእርሱ ጋር ያለንን ኅብረት ፍጹም ወደሚያደርገው ፊት ለፊት ወደሚሆን ራዕይ እንሻገራለን። የዚህ (እግዚአብሔርን የማወቅ) ሕይወት ገጽታዎችም  ሥነ ምግባራዊ፥ ዕውቀታዊ፥ መንፈሳዊ ሲሆኑ   እኛንም በቤተ ክርስቲያን ሕይወታችንና በዓለም ውስጥ በሚኖረን ተግባራችን ውስጥ እንድንሠማራ የሚያደርጉ ናቸው። 

መላ ዘመኑን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት በመመስከር የኖረው ቅዱስ አትናቴዎስ፥ ከነባራዊው ዓለም የተለየና በአመክንዮአዊ ክርክር ላይ ያተኮረ ክርስቲያናዊ ፈላስፋ ወይም ዝም ብሎ የዶግማ ቴዎሎጂያን አልነበረም። ዋና የመከራከሪያ ነጥቡ አበ ነፍሳዊ ( pastoral ) ነበር። የእርሱ ዋና ምኞት የሰዎችን መዳን ማቅረብ ነበር። በመሆኑም የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮና የክርስትና ሕይወት ምን ዓይነት የቀረበ ግንኙነት እንዳላቸው አሳየ ። እንዲህም በማለት አስተማረ፥ 
 « እምነትና እግዚአብሔርን መምሰል እርስ በእርሳቸው የሚተባበሩ እኅትማማቾች ናቸው። በእርሱ የሚያምን እርሱን በመምሰል የሚኖር ነው። እርሱን በመምሰል ሕይወት የሚኖር ደግሞ በእምነቱ የበረታ ነው።» አርዮስን በተከራከረባቸው ጦማሮቹ ሁሉ ያሳየው ነገር ቢኖር በተሰቀለው የእግዚአብሔር ልጅ፥ የእኛ ባሕርይ መቀደሱን፥ መታደሱንና ዳግም መወለዱን ነው። ይህን ሲያመለከት እንዲህ ብሎአል። « 
 እርሱ ራሱን ስለእኛ ከቀደሰ (ዮሐ 17፥18፡19) እና ይህንንም ያደረገው ሰው ሆኖ ከሆነ፥ እንግዲያውስ በዮርዳኖስ በእርሱ ላይ የወረደው መንፈስ ቅዱስ በእኛም ላይ እንደወረደ ግልጽ ነው። የእኛን ሥጋ ገንዘብ አድርጎአልና። እርሱ በተጠመቀ ጊዜ በመንፈስ ቅዱስ እንደተቀባ ከተነገረለት፥ እርሱ ሲጠመቅ በእርሱ እኛም ስለተጠመቅን፥ በእርሱ የተቀባነውም እኛ ነን። » 


የእስክንድርያ ትምህርት ቤት ርዕሳነ መምህራን እና ተማሪዎች አብዛኛዎቹ የድንግልና ሕይወትንም የሚመሩ መላ ሕይወታቸውን ለክርስቶስ የሰጡ ናቸው። እንደምሑራን ብቻ ሳይሆን እንደእውነተኛ መንፈሳውያን፥ ገዳማውያንና ሰባክያን የሚኖሩ ነበሩ። ሕይወታቸውን ለመስጠትና ስለ ክርቶስ የመመስከርና እርሱን የማገልገል ኃላፊነታቸውን ሳይረሱ የእግዚአብሔር ቃል በማጥናት ስለእግዚአብሔር ለማሰላሰል በጣም ይጓጉ ነበር። የእግዚአብሔርን ቃል ለማጥናት ሕይወቱን የሰጠው አርጌንስ ብዙ አሕዛብን በትምህርቱ በመሳብ ወደ ክርስትና እንዲገቡ ማድረጉ ብቻ ሳይሆን እነዚህ ከአሕዛብነት ወደ ክርስትና የገቡት ኋላ በሰማዕትነት ማለፋቸው እንግዲያውስ  አለምክንያት አይደለም። ይህ ክርስቶስ ሁሉ በሁሉ የሆነበት ሕይወት ብዙዎች የትምህርት ቤቱ ርዕሳነ መምህራን ፓትርያርክ ሆነው በመመረጥ ቤተ ክርስቲያንን በሚገባ እንዲመሩ አስችሎአቸዋል። 



Tuesday, March 5, 2013

ጸሎተ ስምዖን ዓምዳዊ ክፍል 9

ምዕራፍ ፳፭፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ የአንተን ደስታ ሙላብኝ። አንተ ሐዘን የማያገኘው ደስታ ነህና። በነፍሴ ውስጥ አገኘው ዘንድ ይህን ደስታ ስጠኝ። ነፍሴ ንጹህ ማደሪያና ምርጥ ዕቃ ትሁን። ልቤ ታቦትህ ሕሊናዬም ምሥዋዕ  ይሁንልህ። ብርሃናውያን የሆኑ የመላእክትህን ምስጋና ያሰማ። ልቡናዬ ከፍ ካለው የመላእክት የምስጋና ድምጽ ጋር ይዋሃድ። 
ምዕራፍ ፳፮፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ ፍጥረትን በተሐድሶ አዲስ ለማድረግ የመጣህ፥ በምሕረትህ አድሰኝ። 
ምዕራፍ ፳፯፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ ራስህን በዮሐንስ ፊት ዘንበል (ዝቅ) ያደረግህ፥ ለክብርህ በሚገባ ምስጋና ከፍ ከፍ አደርግህ ዘንድ፥ ኃጢአት ከብዶት ዘንበል ያለውን ራሴን ከፍ አድርግልኝ። 

Friday, March 1, 2013

የእስክንድርያ ትምህርት ቤት (ክፍል አራት)


የእስክንድርያ ትምህርት ቤት 
በቀሲስ ቴድሮስ ማላቲ 
ትርጉም በሊቀ ኅሩያን ቀሲስ መልአኩ ባወቀ ተረፈ 

ክፍል አራት 

የእስክንድርያ ቴዎሎጂ መለያ ባህርያት 

ስለ ቅዱሳት መጻሕፍት ትርጓሜ፥ ስለፍልስፍና እና ስለ ዕውቀት (ግኖሲስ) የእስክንድርያ ትምህርት ቤት ያለውን ዕይታ፥ በሌሎች ምዕራፎች ላይ የምንመለስ ሲሆን አሁን ግን የእስክንድርያ ትምህርት ቤትን መለያ ባህርያትን እናያለን። 

1.የመለኮታዊ ባህርይ ተካፋይነት (Deification) ወይም የተሐድሶ ጸጋ  (The grace of renewal)

ብዙዎች ምሑራን እንደሚስማሙበት የእስክንድርያ ነገረ መለኮት እምብርት የመለኮታዊ ባህርይ ተካፋይነት ወይም የተሐድሶ ጸጋ ነው። የመለኮታዊ ባህርይ ተካፋይነት  ማለት በወደቀው የሰው ባህርይ ፈንታ የሰው ባህርይ በአጠቃላይ ታድሶ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ባህርይ ተካፋይ መሆኑ ነው። ወይም ሐዋርያቱ እንደአስተማሩት አማኝ « የመለኮቱ ባህርይ ተካፋይ» መሆኑ(2 ጴጥ 1፥4) ወይም በእግዚአብሔር ምሳሌ አዲሱ ሰው ሲሆን ነው። ( ቆላ 3፥10)  ይህ የነገረ መለኮት አስተሳስሰብ እስክንድርያዎችን በነገረ መለኮት ቃላቶችና ብያኔዎች ዙሪያ ከሚደረግ ክርክር በማራቅ በመንፈስ ቅዱስ ሥራ ከእግዚአብሔር አብና ከአንድ ልጁም ከወልድ ከኢየሱስ ጋር  አንድ በመሆን የመለኮትን ጸጋ ለማግኘት ወይም የወደቀውን ባህርያችንን ካደሰው ከክርስቶስ ጋር አንድ መሆን ላይ እንዲያተኩሩ አስችሎአቸዋል።   

ስለዚህ ከሰማይ ወረደ 
ስለዚህም የሰውን ባህርይ ገንዘብ አደረገ፤ 
ስለዚህም የሰውን መከራ ለመታገስ ፈቃደኛ ሆነ
በደካማነታችን መጠን ዝቅ በማለት፤ በኃይሉ መጠን ከፍ አደረገን፤
የእግዚአብሔር ቃል ሰው ሆነ፤ ሰው እንዴት አምላክ እንደሚሆን  ትማሩ ዘንድ። 
ቀሌምንጦስ ዘእስክንድርያ

የእስክንድርያ አባቶች የነገረ መለኮት አስተሳሰባቸው በመላ ያተኮረው በእግዚአብሔር ጸጋ ላይ ነው። የእግዚአብሔር ጸጋ፥ በመንፈስ ቅዱስ አማካይነት ከአብና ከወልድ ጋር ኅብረትን የሚሰጠን ባህያችንን የሚለውጥ የተሐድሶ ጸጋ  ይኸውም ከእግዚአብሔር ጋር የሚሆን አንድነትና ኅብረት ነው። በክርስቶስ ኢየሱስ ያገኘነው በመንፈስ ቅዱስ የሆነ የኃጢአት ይቅርታን ብቻ ሳይሆን ነገር ግን " አዲስ ሕይወት"  አግኝተናል። ይህም አዲስ ሕይወት ከኃጢአት ነጻ የሆነ መለኮታዊ ጸጋ ነው። ቅዱስ ጳውሎስ «አሮጌውን ሰው አስወግዱ» ወይም የተበላሸውን ባህርይ አስወግዱ፥ ነገር ግን በመንፈስ ቅዱስ የታደሰውን አዲሱን ተፈጥሮ ወይም በእግዚአብሔር ጽድቅና ቅድስና የተፈጠረውን አዲሱን ሰው " ውስጣዊን ሰው" ልበሱ ይለናል። 2 ቆሮ 5፥21፤ ሮሜ 8፥1) በመለኮታዊ ጸጋው የክርስቶስ አካል አባላት፥ የእግዚአብሔር ልጆች፥ እና የቅድስና ሕይወትን እንድንኖር እንድንኖር ኃይልን የተቀበልን ነን። ምክንያቱም በክርስቶስ ተቀድሰናል፥ ወደ አብም ቀርበናል። አማኝ በሁለንተናው፥ በነፍሱ፥ በአካሉ፥ በስሜቱና በአእምሮው የጽድቅ መሣሪያ ለመሆን ተቀድሶአል። (ሮሜ 6፥13) ከሙታን የተነሣው ክርስቶስ በአማኙ ሕይወት ውስጥ መለኮታዊ ሥጦታ ሆኖ ይገኛል። ዘላለማዊና ሰማያዊ ክብርን እንደሚገባለት ሁሉ ፥ አሁን ለአማኙ ውስጣዊ ክብር ይሰጠዋል።  
ይህ የሰው ተፈጥሮ መታደስ ነው " የመለኮታዊ ክብር ተካፋይነት" የሚባለው። ይህም የተባለው መለኮታዊ ባህርዩን ስለሚያካፍልና ክርስቶስን የእኛ ጽድቅና ቅድስና አድርጎ ስለሚቀበል ነው። ( 2 ጴጥ 1፥4፤ 1 ቆሮ 1፥30) የእስንድርያ ነገረ መለኮት በሚከተሉት ቃላት ተጠቅልሎ ሊገለጥ ይችላል:- " እግዚአብሔር ሰውነትን ወሰደ፤ ሰው ሕይወቱን ይጋራ ዘንድ።" ወይም " እግዚአብሔር ሰው ሆነ፤ ሰዎች አማልክት ይሆኑ ዘንድ" 

ጆሴፍ ስቲለር እንደተናገረው ምዕራቡ የክርስትና ክፍልና ምስራቁ ክፍል የክርስቶስን ሥራ የሚገልጡት በተለያየ መንገድ ነው። በምዕራቡ ዓለም የክርስቶስ ሥራ ከኃጢአት በመቤዠት ላይ ያተኮረ ነው። በምሥራቅ ደግሞ የክርቶስ ሥራ ሰውን በማክበር ላይ ያተኮረ ነው። የምዕራቡ ትምህርት የመዋጀት ትምህርት (The doctrine of atonement) ማዕከላዊ ትምህርት ነው፤ በአንጻሩ በምሥራቁ ደግሞ ሱታፌ፥ አብርሆት፥ እና መለወጥ ነው። የምዕራቡ አዳኝ የምስራቁ ፓቶክራቶር (አኃዜ ኩሉ) ነው።