Tuesday, June 19, 2012

የሕጉ ተግባር ምንድነው? ካለፈው የቀጠለ



19 እንግዲህ ሕግ ምንድር ነው? ተስፋው የተሰጠው ዘር እስኪመጣ ድረስ በመካከለኛ እጅ በመላእክት በኩል ስለ ሕግ መተላለፍ ተጨመረ።20 መካከለኛውም ለአንድ ብቻ አይደለም እግዚአብሔር ግን አንድ ነው።21 እንግዲህ ሕግ የእግዚአብሔርን የተስፋ ቃል የሚቃወም ነውን? አይደለም። ሕያው ሊያደርግ የሚቻለው ሕግ ተሰጥቶ ቢሆንስ በእውነት ጽድቅ ከሕግ በሆነ ነበር፤22 ነገር ግን በኢየሱስ ክርስቶስ ከማመን የሆነው የተስፋ ቃል ለሚያምኑ ይሰጥ ዘንድ መጽሐፍ ከኃጢአት በታች ሁሉን ዘግቶታል። 23 እምነትም ሳይመጣ ሊገለጥ ላለው እምነት ተዘግተን ከሕግ በታች እንጠበቅ ነበር።24 እንደዚህ በእምነት እንጸድቅ ዘንድ ሕግ ወደ ክርስቶስ የሚያመጣ ሞግዚታችን ሆኖአል፤25 እምነት ግን መጥቶአልና ከእንግዲህ ወዲህ ከሞግዚት በታች አይደለንም።26 በእምነት በኩል ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጆች ናችሁና፤27 ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋልና።28 አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፥ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፥ ወንድም ሴትም የለም፤ ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና።29 እናንተም የክርስቶስ ከሆናችሁ እንኪያስ የአብርሃም ዘር እንደ ተስፋውም ቃል ወራሾች ናችሁ።
የሕጉ ዓላማ ምንድነው? 
ስለ ሕጉ ጳውሎስ የሚመልሰውን ከማየታችን በፊት ሕጉ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያለው ሚና ምንድነው? ለዚህ ሦስት ዓይነት አስተያየቶች በዘመናችንም ሆነ ከጥንት ዘመን ጀምሮ ተሰጥተዋል::
1. የክርስቶስ መምጣት ሕጉን ሙሉ በሙሉ ሽሮት የመንፈስ ቅዱስ ዘመን ታውጆአል የሚል ነው:: 
ይህ ብዙ ጊዜ ከነ መርቅያን (ማርስዮንና) ከሌሎች አንቲኖሚያንስ ጋር ቢያያዝም የተወሰነ ክርስቲያናዊ እውነት አለው:: 
2. ሕጉ የመጀመሪያው የእግዚአብሔር የተገለጠው ፈቃድ ቢሆንም የተሙዋላ (ፍጹሙ) ፈቃዱ ግን አይደለም:: የእግዚአብሔር ፈቃድ ሙሉ በሙሉ በክርስቶስ ተገልጦ ለእኛ ደግሞ በአዲስ ኪዳን ትምህርት በመንፈስ ቅዱስ ተሰጥቶአል:: 
3. የሙሴ ህግ ለቤተ ክርስቲያንም የተሰጣት የተገለጠው የእግዚአብሔር ሕግ ነው:: ሆኖም የሕጉን ፈቃድ መፈጸም የሚቻለው በክርስቶስ በማመን በምንቀበለው በክርስቶስ መንፈስ ነው የሚል ነው:: 
ሕግ ምንድነው? 
1. በኅብረተሰብ መካከል ሥነ ምግባርን የሚያስጠብቅ መመሪያ ነው:: 
2. በታሪክና በሰው ሕይወት ኃጢአትን በመግለጥ ሰውን ወደ እግዚአብሔር ጸጋ የሚመራ የእግዚአብሔር መሣሪያ ነው:: 
3. በቤተ ክርስቲያን የክርስቲያን ሥነ ምግባር መመሪያ ነው:: 
ይህ ሦስተኛው የሕግ አጠቃቀማችን (ሰርሺየስ ዩዘስ ሌጊስ ) ነው ብዙ ጊዜ ክርክር ውስጥ የሚያስገባን:: 
1. የሕጉ ዓላማ ምንድነው? 
1.1. በበደል ምክንያት የተጨመረ ነው:: 
ይህም ኃጢአት በመግባቱ መጨመሩን ወይም ኃጢአት ስለገባ ኃጢአትን ለመግለጥ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለመግለጽ የተጨመረ ነው:: 
1.2. የተስፋው ዘር እስኪመጣ የተሰጠ ነው:: 
1.3. በፍጡራን መካከለኛነት (በሙሴና በመላእክት) የተሰጠ ነው:: 
2. ሕጉ ለአብርሃም የተሰጠውን ተስፋ ይቃወማልን? አለበለዚያ ለምን ተሰጠ? 
3. ሕጉ ሕይወትን የሚሰጥ ሕግ አልሆነም:: 
4. በክርስቶስ ያመንን ሁላችን የእግዚአብሔር ልጆች ሆነናል:: ምክንያቱም በክርስቶስ ያመንን እኛ ክርስቶስን ስለለበስን ነው:: 
5.በክርስቶስ ያመኑ ጾታ ዘር ወገን ሳይለያቸው ሁሉም አንድ ናቸው እውነተኞቹ የአብርሃም ዘር ወራሾች ናቸው:: 

ልጆች ነን   4:1- 31 
እዚህ ላይ ስለልጅነታችን ይህ መልእክትና እንዲሁም ሌሎችም የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች የሚያስተምሩንን መመልከት ይገባል:: 
1.ልጅነታችን የተመሠረተው እግዚአብሔር ለእኛ ባለው የዘላለም ፍቅር ነው:: ኤፌሶን 1:4-6:: 
1.1 እግዚአብሔር አብ አስቀድሞ ዓለም ሳይፈጠር በዘላለም ፍቅር ወደደን 
1.2 እግዚአብሔር ወልድ እኛ የእግዚአብሔር ልጆች እንሆን ዘንድ እርሱ ሰው ሆነ ሮሜ 8:29
1.3 እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በእኛ ውስጥ በማደር አባ አባት የምንልበት የልጅነት መንፈስ ሆነን:: ሮሜ 8:1-11:: 
2. ይህን ልጅነታችንን የምናገኘው በክርስቶስ በማመን ነው::ዮሐ 1:12::  ኤፌሶን 2:1-10:: 
3. ይህ ልጅነት ዘር ወገን ጾታ የማይለይ ለሁሉም የተሰጠ ነው:: 
ይህ ልጅነት በመንፈስ ቅዱስ የታተመ ስለሆነ ዋስትና ያለው ልጅነት ነው:: ሮሜ 8:16:: 
ሀ.  በክርስቶስ የተገኘው ልጅነትና የልጁ መንፈስ 4:1-7

1 ነገር ግን እላለሁ፥ ወራሹ ሕፃን ሆኖ ባለበት ዘመን ሁሉ፥ ምንም የሁሉ ጌታ ቢሆን ከቶ ከባሪያ አይለይም፥2 ነገር ግን አባቱ እስከ ቀጠረለት ቀን ድረስ ከጠባቂዎችና ከመጋቢዎች በታች ነው።3 እንዲሁ እኛ ደግሞ ሕፃናት ሆነን ሳለን ከዓለም መጀመሪያ ትምህርት በታች ተገዝተን ባሪያዎች ነበርን፤4 ነገር ግን የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን ከሕግም በታች የተወለደውን ልጁን ላከ፤5 እንደ ልጆች እንሆን ዘንድ፥ ከሕግ በታች ያሉትን ይዋጅ ዘንድ።6 ልጆችም ስለ ሆናችሁ እግዚአብሔር አባ አባት ብሎ የሚጮኽ የልጁን መንፈስ በልባችሁ ውስጥ ላከ።7 ስለዚህ ከእንግዲህ ወዲህ ልጅ ነህ እንጂ ባሪያ አይደለህም፤ ልጅም ከሆንህ ደግሞ በክርስቶስ የእግዚአብሔር ወራሽ ነህ።
1. የሕጻንነት ዘመን በሕግ ሞግዚትነት የነበርንበት ዘመን ነው:: 
2. ከሕግ በታች ያለነውን ይዋጀን ዘንድ እግዚአብሔር ልጁን ላከልን:: 
3. ልጅነታችንን ያስረግጥ ዘንድ የልጁን መንፈስ በልባችን ላከው:: 
4. ልጆች እንጂ ባሮች አይደለንም:: ልጆች በመሆናችን በክርስቶስ የእግዚአብሔር ወራሾች ነን:: 
ለ. እውነተኛ አምላክና ሐሰተኛ አማልክት 4:8-11
ነገር ግን በዚያን ጊዜ እግዚአብሔርን ሳታውቁ በባሕርያቸው አማልክት ለማይሆኑ ባሪያዎች ሆናችሁ ተገዛችሁ፤9 አሁን ግን እግዚአብሔርን ስታውቁ ይልቅስ በእግዚአብሔር ስትታወቁ እንደ ገና ወደ ደካማ ወደሚናቅም ወደ መጀመሪያ ትምህርት እንዴት ትመለሳላችሁ? እንደ ገና ባሪያዎች ሆናችሁ ዳግመኛ ለዚያ ልትገዙ ትወዳላችሁን?10 ቀንንና ወርን ዘመንንም ዓመትንም በጥንቃቄ ትጠብቃላችሁ።11 ምናልባት በከንቱ ለእናንተ ደክሜአለሁ ብዬ እፈራችኋለሁ።
1. ዓላማውን የፈጸመውን ሕግ እንደገና የአምልኮ መንገድ ማድረግ ወደባርነት መግባት ነው:: 
2. የገላትያ ክርስቲያኖች በወንጌል የተሰጣቸውን ነጻነት ወይም ባርነትን ይመርጡ እንደሆነ ምርጫቸውን ማስተካከል አለባቸው:: 
  1. እስራኤላውያን ከነጻነት ይልቅ ባርነትን መምረጣቸው ምን እንዳስከተለባቸው ያሳስባቸዋል:: ዘጸአት 14:11-12:: 16:3:: 17:3:: ዘኁልቍ 14:1-4:: 
  2. ጳውሎስን ያሳዘነው የገላትያ ክርስቲያኖች የአይሁድን በዓላት ማክበራቸው ሳይሆን የሚያከብሩበት መንገድ ነው:: ሐዋ 20:6;1 ቆሮ 16:8:: 
ሐ. የጳውሎስ ልመና 4:12-20

12 ወንድሞች ሆይ፥ እኔ ደግሞ እንደ እናንተ ሆኜአለሁና። እንደ እኔ ሁኑ ብዬ እለምናችኋለሁ። አንዳችም አልበደላችሁኝም።13 በመጀመሪያ ወንጌልን በሰበክሁላችሁ ጊዜ ከሥጋ ድካም የተነሣ እንደ ነበረ ታውቃላችሁ፥14 በሥጋዬም ፈተና የሆነባችሁን ነገር አልናቃችሁትምና አልተጸየፋችሁትም ነገር ግን እንደ እግዚአብሔር መልአክ አዎን እንደ ክርስቶስ ኢየሱስ ተቀበላችሁኝ።15 እንግዲህ ደስ ማሰኘታችሁ ወዴት አለ? ቢቻልስ ዓይኖቻችሁን አውጥታችሁ በሰጣችሁኝ ብዬ እመሰክርላችኋለሁ።16 እንኪያስ እውነቱን ስለ ነገርኋችሁ ጠላት ሆንሁባችሁን?17 በብርቱ ይፈልጉአችኋል፥ ለመልካም አይደለም ነገር ግን በብርቱ ትፈልጉአቸው ዘንድ በውጭ ሊያስቀሩአችሁ ይወዳሉ።18 ነገር ግን ከእናንተ ዘንድ በምኖርበት ጊዜ ብቻ ሳይሆን ሁልጊዜ በመልካም ነገር ተፈላጊ ብትሆኑ መልካም ነው።19 ልጆቼ ሆይ፥ ክርስቶስ በእናንተ እስኪሣል ድረስ ዳግመኛ ስለ እናንተ ምጥ ይዞኛል።20 ስለ እናንተ አመነታለሁና አሁን በእናንተ ዘንድ ሆኜ ድምፄን ልለውጥ በወደድሁ።
1. ጳውሎስ ለገላትያ ሰዎች ለእርሱ የነበራቸውን የቀደመ ፍቅራቸውን እንዲያስቡ ያሳስባቸዋል:: 
2. አሁን እያሳሳቱአቸው ያሉ ሰዎች ዓላማ እነርሱን ከእግዚአብሔር መንግሥት ውጭ ለማስቀረት ነው:: 
3. የጳውሎስ ጭንቀት ደግሞ ክርስቶስ በእነርሱ ሕይወት ክርስቶስ እስኪሳል ነው:: 
መ. ይስሐቅና እስማኤል የአብርሃም ሁለት ልጆች 4:21-31

21 እናንተ ከሕግ በታች ልትኖሩ የምትወዱ፥ ሕጉን አትሰሙምን? እስኪ ንገሩኝ።22 አንዱ ከባሪያይቱ አንዱም ከጨዋይቱ የሆኑ ሁለት ልጆች ለአብርሃም እንደ ነበሩት ተጽፎአልና።23 ነገር ግን የባሪያይቱ ልጅ እንደ ሥጋ ተወልዶአል፥ የጨዋይቱ ግን በተስፋው ቃል ተወልዶአል።24 ይህም ነገር ምሳሌ ነው፤ እነዚህ ሴቶች እንደ ሁለቱ ኪዳኖች ናቸውና። ከደብረ ሲና የሆነችው አንዲቱ ለባርነት ልጆችን ትወልዳለች፥ እርስዋም አጋር ናት።25 ይህችም አጋር በዓረብ ምድር ያለችው ደብረ ሲና ናት፤ አሁንም ያለችውን ኢየሩሳሌምን ትመስላለች፥ ከልጆችዋ ጋር በባርነት ናትና።26 ላይኛይቱ ኢየሩሳሌም ግን በነጻነት የምትኖር ናት እርስዋም እናታችን ናት።27 አንቺ የማትወልጅ መካን፥ ደስ ይበልሽ፤ አንቺ አምጠሽ የማታውቂ፥ እልል በዪና ጩኺ፤ ባል ካላቱ ይልቅ የብቸኛይቱ ልጆች በዝተዋልና ተብሎ ተጽፎአል።28 እኛም፥ ወንድሞች ሆይ፥ እንደ ይስሐቅ የተስፋ ቃል ልጆች ነን። 29 ነገር ግን እንደ ሥጋ የተወለደው እንደ መንፈስ የተወለደውን በዚያን ጊዜ እንዳሳደደው ዛሬም እንዲሁ ነው።30 ነገር ግን መጽሐፍ ምን ይላል? የባሪያይቱ ልጅ ከጨዋይቱ ልጅ ጋር አይወርስምና ባሪያይቱን ከልጅዋ ጋር አውጣት።31 ስለዚህ፥ ወንድሞች ሆይ፥ የጨዋይቱ ልጆች ነን እንጂ የባሪያይቱ አይደለንም።
ሕግ                              ወንጌል 
የአጋር ቃል ኪዳን        የሳራ ቃል ኪዳን 
እስማኤል  (ሥጋ)        ይስሐቅ (ተስፋ) 
አሳዳጅ                     ተሳዳጅ
የባርነት ልጆች            የነጻነት ልጆች 
ሲና ተራራ                 ጽዮን ተራራ (ጎልጎታ? መንግሥተ ሰማይ 
ምድራዊቱ ኢየሩሳሌም  ሰማያዊቱ ኢየሩሳሌም 
አሮጌው ኪዳን             አዲሱ ኪዳን
1.  ሁለቱ ሴቶች አንደኛዋ ባሪያ ሌላዋ ጨዋ ተደርገው ተገልጠዋል:: 
2. የሁለቱ ልጆች አንደኛው በተስፋ የተወለደ ሁለተኛው ደግሞ ባለማመን በሥጋ የተወለደ ተደርጎ ተወስዶአል:: 
3. ጳውሎስ በአጋር ታሪክ ደብረ ሲናንና ኢየሩሳሌምን በማያያዝ በሕጉ ሥር ለሚኖሩ የባርነት ምሳሌ አደረጋቸው:: 
4. ሳራን ደግሞ ከሰማያዊቱ ኢየሩሳሌም ጋር በማገናኘት ከእርሱዋ የሚወለዱ የመካኒቱ ልጆች (ኢሳ 51:2 እና 54:1 ተመልከቱ) ከሕጉ ነጻ የሆኑ የነጻነት ልጆች አደረጋቸው:: 
5. የአጋር ልጅ የሳራን ልጅ እንዳሳደደው ወደ ይሁዲነት ለመውሰድ የሚፈልጉ በክርስቶስ ያሉትን እያሳደዱ ናቸው:: 
ስንሰደድ ምን እናድርግ? 
1. ክርስቶስ ምሳሌያችን እንደሆነ እናስብ::
2. ከእኛ በፊት ብዙ ቅዱሳን እንደተሰደዱ እናስብ:: 
3. እግዚአብሔር ሁሉን ነገር ወደ ፍርድ እንደሚያመጣ እናስብ:: 

Tuesday, June 5, 2012

የተቀበልነው ስጦታ 3:1-29



1. የእምነት በቂነት 3:1-5 
የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች ሆይ፥ በዓይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር፤ ለእውነት እንዳትታዘዙ አዚም ያደረገባችሁ ማን ነው? 2 ይህን ብቻ ከእናንተ እንድማር እወዳለሁ፤ በሕግ ሥራ ወይም ከእምነት ጋር በሆነ መስማት መንፈስን ተቀበላችሁን? 3 እንዲህን የማታስተውሉ ናችሁ? በመንፈስ ጀምራችሁ አሁን በሥጋ ትፈጽማላችሁን? 4 በውኑ ከንቱ እንደ ሆነስ እንደዚህ ያለ መከራ በከንቱ ተቀበላችሁን? 5 እንግዲህ መንፈስን የሚሰጣችሁ በእናንተም ዘንድ ተአምራት የሚያደርግ፥ በሕግ ሥራ ነውን ወይስ ከእምነት ጋር በሆነ መስማት ነው?
1. የገላትያ ሰዎች የማያስተውሉ እንዲሆኑ በሌሎች ተጽዕኖ ሥር ወድቀዋል:: 
2. ባለማስተዋላቸው ከክርስቶስ የማዳን ሥራ ጋር መቃረን ጀምረዋል::  
3. ባለ ማስተዋላቸው በእነርሱ ውስጥ ያለውን የመንፈስ ቅዱስ ሥራ መቃረን ጀምረዋል:: 
3.1 የክርስትናቸውን ጅማሬ ያገኙት በእምነት ከሆነ መስማት በሆነ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ነው:: ሮሜ 8:9:: 
3.2 መንፈስ ቅዱስ በመካከላቸው ሆኖ የሚሰራው ከእምነት ጋር በሆነ መስማት ነው:: 
       ልጅነትን በማስረገጥ- ሮሜ8:15-16:: 
       ተአምራትን በማደረግ  
       ፍቅርንና የመንፈስ ፍሬዎችን በመስጠት 
4. ከእምነት በሚገኝ በመንፈስ ቅዱስ ከጀመራችሁ በሕግ ሥራ በሚገኝ በሥጋ አትፈጽሙ:: ሮሜ 8:13:: 
2. የአብርሃም ምሳሌነት 3:6-9
እንዲሁ አብርሃም በእግዚአብሔር አመነና ጽድቅ ሆኖ ተቆጠረለት። 7 እንኪያስ ከእምነት የሆኑት እነዚህ የአብርሃም ልጆች እንደ ሆኑ እወቁ። 8 መጽሐፍም እግዚአብሔር አሕዛብን በእምነት እንዲያጸድቅ አስቀድሞ አይቶ። በአንተ አሕዛብ ሁሉ ይባረካሉ ብሎ ወንጌልን ለአብርሃም አስቀድሞ ሰበከ። 9 እንደዚህ ከእምነት የሆኑት ካመነው ከአብርሃም ጋር ይባረካሉ።
1. አብርሃም ጽድቅን ያገኘው በእምነት ነው:: ዘፍ 15:6:: 
2. የአብርሃም የሆኑት ሁሉ የአብርሃምን ጽድቅ የሚያገኙት በአብርሃም እምነት በኩል ነው:: ዘፍ12:2
3. አብርሃምንና በእምነት ልጆቹ የሆኑትን አሕዛብን የሚያገናኛቸው ሁለቱም ያመኑበት ወንጌል ነው:: 
3.1 የአብርሃም ልጆች መሆን ለአይሁድ ብቻ ሳይሆን ለሁሉም የተሰጠ ነው:: 
3.2 የአብርሃም ልጆች መሆን አብርሃምን መምሰል ከእኛ የሚጠብቅ ነው:: ዮሐ 8:39::
3.3 የአብርሃም ልጆች መሆን ማለት የአብርሃምን በረከት ወራሾች መሆን ማለት ነው:: ገላ 3:29:: 
4. በእምነት የሚገኘው ጽድቅ በእግዚአብሔር ፊት ልጅነታችንን ለማግኘት መሰረት ነው:: 
4.1 ጽድቃችን የአብርሃም ልጆች በመሆናችን የምናገኘው ውርስ ነው:: ይህም የኃጢአትን ፍርሃት በማስወገድ እውነተኛ የሆነ ሕብረት ከእግዚአብሔር ጋር እንዲኖረን ያደርጋል:: 
4.2 ለቤዛ ቀን የሚያትመን የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ የአብርሃም ልጆች በመሆናችን የምናገኘው ውርስ ነው:: ይህም የሞትን ፍርሃት የዘላለምን ሕይወት ተስፋ በማድረግ ይተካዋል:: 
3. ከሕግ እርግማን ነጻ መውጣት 3:10-14
ከሕግ ሥራ የሆኑት ሁሉ በእርግማን በታች ናቸውና፤ በሕግ መጽሐፍ በተጻፉት ሁሉ ጸንቶ የማይኖር የማያደርግም ሁሉ የተረገመ ነው ተብሎ ተጽፎአልና። 11 ጻድቅ በእምነት ይኖራል ተብሎአልና ማንም በእግዚአብሔር ፊት በሕግ እንዳይጸድቅ ግልጥ ነው። 12 ሕግም ከእምነት አይደለም ነገር ግን። የሚያደርገው ይኖርበታል ተብሎአል። 13 በእንጨት የሚሰቀል ሁሉ የተረገመ ነው ተብሎ ተጽፎአልና ክርስቶስ ስለ እኛ እርግማን ሆኖ ከሕግ እርግማን ዋጀን፤ 14 የመንፈስን ተስፋ በእምነት እንድንቀበል፥ የአብርሃም በረከት ወደ አሕዛብ በኢየሱስ ክርስቶስ ይደርስላቸው ዘንድ።
1. ከሕግ ሥራ የሆኑት ሁሉ በእርግማን በታች ናቸው:: 
2. ክርስቶስ ከሕግ እርግማን ዋጅቶናል:: 2 ቆሮ 5:21:: ኢሳ 53:4-6
3. ክርስቶስ ከሕግ እርግማን የዋጀን የመንፈስን ተስፋ በእምነት እንድንቀበል ነው::  
4. ዘርና መካከለኛ የሆነው ክርስቶስ 3:15-22
ወንድሞች ሆይ፥ እንደ ሰው ልማድ እላለሁ። የሰው ስንኳ ቢሆን እርግጠኛውን ኪዳን ማንም አይንቅም ወይም አይጨምርበትም።16 ለአብርሃምና ለዘሩም የተስፋው ቃል ተነገረ። ስለ ብዙዎች እንደሚነገር። ለዘሮቹም አይልም፤ ስለ አንድ እንደሚነገር ግን። ለዘርህም ይላል፥ እርሱም ክርስቶስ። 17 ይህንም እላለሁ፤ ከአራት መቶ ሠላሳ ዓመት በኋላ የተሰጠው ሕግ አስቀድሞ በእግዚአብሔር የተረጋገጠውን ኪዳን የተስፋውን ቃል እስኪሽር ድረስ አያፈርስም። 18 ርስቱ በሕግ ቢሆንስ እንግዲያስ በተስፋ ቃል አይሆንም፤ በተስፋ ቃል ግን እግዚአብሔር ለአብርሃም ሰጥቶአል።19 እንግዲህ ሕግ ምንድር ነው? ተስፋው የተሰጠው ዘር እስኪመጣ ድረስ በመካከለኛ እጅ በመላእክት በኩል ስለ ሕግ መተላለፍ ተጨመረ። 20 መካከለኛውም ለአንድ ብቻ አይደለም እግዚአብሔር ግን አንድ ነው። 21 እንግዲህ ሕግ የእግዚአብሔርን የተስፋ ቃል የሚቃወም ነውን? አይደለም። ሕያው ሊያደርግ የሚቻለው ሕግ ተሰጥቶ ቢሆንስ በእውነት ጽድቅ ከሕግ በሆነ ነበር፤ 22 ነገር ግን በኢየሱስ ክርስቶስ ከማመን የሆነው የተስፋ ቃል ለሚያምኑ ይሰጥ ዘንድ መጽሐፍ ከኃጢአት በታች ሁሉን ዘግቶታል። 
1. ለአብርሃምና ለዘሩ የተሰጠው ተስፋ ዘላለማዊ ተስፋ ነው:: 
2. የአብርሃም ዘር የተባለው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው:: 
3. ለአብርሃምና ለዘሩ የተሰጠውን ተስፋ ከ430 ዓመት በኋላ የመጣው የሙሴ ሕግ አልሻረውም::
3.1 ሕጉ የተሰጠው ኃጢአትን ለመግለጥ ነው::ሮሜ 4:15::
3.2 ሕጉ የተሰጠው የኃጢአትን አስከፊነት በማሳየት ሰዎችን ወደ ጸጋ ለማድረስ ነው:: ሮሜ 5:20::