Monday, October 31, 2011

ኢየሩሳሌም ኢየሩሳሌም ሉቃ 13:31-35

ፈሪሳውያን ለጌታ ኢየሱስ በማሰብ (አንዳንድ ደግ ፈሪሳውያን አይጠፉምና) ሄሮድስ ሊግድልህ ስለሚፈልግ እባክህ ከዚህ ዘወር በል ብለውት ሲመክሩት እናያለን:: ነገሥታት በምድራዊ ሥልጣናቸው ሥር ብዙ የሚታዘዝ ኃይል ስላላቸው የሚያስፈሩ ሊመስሉ ይችላሉ:: ሆኖም ግን የሥልጣናት ሁሉ ጌታ የሆነው እርሱ ሥልጣን ላላቸው የሚናገር ነው:: በመሆኑም ሄሮድስ በጌታ ኢየሱስ ሕይወት ላይ ሥልጣን እንደሌለውና ነገር ግን በአባቱ ፈቃድና በራሱ ፈቃድ ሞቱ በኢየሩሳሌም እንደሚሆን ይናገራል:: ሆኖም ግን የጌታን ልብ የሰበረው በተንኮሉና በክፋቱ በነፍሰ ገዳይነቱ ቀበሮ የተባለው የሄሮድስ ጌታን ለመግደል መሞከሩ ሳይሆን የኢየሩሳሌም መሲሁንና አዳኟን አለመቀበልዋ ነበር:: ዶሮ ጫጩቶቹዋን ከጭልፊት እንደምትሰውር በክንፎችዋ ከብርድ ሰውራ ሙቀት እንደምትሰጥ ጌታም ኢየሩሳሌምን ከሚመጣባት ፍርድ ለመሰወር ምን ያህል እንደፈለገና ነገር ግን ኢየሩሳሌም የጌታን ፍቅርን ለመቀበል እምቢተኛ እንደሆነች ይነግረናል::

ኢየሩሳሌም የአምላኩዋን ፍቅር እምቢ ብላ መግፋትዋ በስተኋላ በ70 ዓም ፍራሽ በፍራሽ እንድትሆን ልጆቹዋም በመላው ዓለም እንዲበተኑ አድርጎአል:: የጌታንም ልብ የሰበረው ይህ ሊመጣ ያለው የእግዚአብሔርን ፍርድ ለማየት አለመቻላቸው ነበር::

በአመዛኙ በሃይማኖታዊ ህይወታችን ብዙ የምንጨነቀው እግዚአብሔርን የምናስድስትባቸው ብለን ስላዘጋጀናቸው ነገሮች ነው:: ይህ ሁሉ ጥሩ ሆኖ ግን እኛው ባቆምናቸው ህጎች ወጎችና ሥርዓቶች ተውጠን ስንቀር ግን እግዚአብሔር ያዘጋጀልንን መልካም ነገር ለማየት ያቅተናል:: ዋናውን ነገር እንረሳዋለን:: ሌት ተቀን በጾም ሰውነታቸውን የሚያደክሙ ነገር ግን ወንድማቸውን ይቅር ለማለት የማይችሉ ሰዎች ብዙዎች ናቸው:: እንደ አገሬ ደብተራ ማኅሌተ እግዚአብሔርን አደርሳለሁ ብሎ በአምላኩ ፊት ቆሞ እርሱ ግን በዜማው ወዝ ምክንያት ከጓደኛው ጋር በመቋሚያ ይደባደባል:: ዋናውን ነገር መርሳት በትንሹ ነገር ላይ ዋጋ መክፈልን ያመጣል::

አምላኬ ከልቤ ይልቅ ቅርብ እንደሆነ ሳስተውል ከምንም በላይ ላደርግ የሚገባኝ ነገር ቢኖር የእርሱን ፍቅር የእርሱን ምህረት ለመቀበል ልቤን ማዘጋጀት ነው::

Saturday, October 29, 2011

ጌታ ሆይ የሚድኑ ጥቂቶች ናቸውን? ሉቃ 13:22-35

በአገራችን የተለመደ ቀልድ አለ:: ሰውዬው ገሃነም ሲወርድ የንስሐ አባቱን ቀድመው ወርደው ያገኛቸዋል:: ደንግጦ አባቴ እርሶም እዚህ ሲላቸው እርሳቸውም ልጄ ዝም ብል ብፁዕ አባታችንም እዚህ ናቸው በማለት ጳጳሱም እዚህ መሆናቸውን ነገሩት:: ቀልድ ነው ነገር ግን ከፍ ያለ ቁም ነገር የያዘ ቀልድ ነው:: ለምዶብን የእግዚአብሔርን መንግሥት በምድራዊ መመዘኛዎችና በአፍአዊ ድርጊቶች ለማስቀመጥ እንሞክራለን:: በመሆኑም ብዙ ጊዜ በእግዚአብሔር ቤት ሥፍራ የምንሰጣቸው ሰዎች በእግዚአብሔር ዘንድ አንዳችም ቦታ የሌላቸውን ነው:: በዚህ ቦታ ጌታ ከባድ ጥያቄ ተጠይቆአል:: የሚድኑት ጥቂቶች ናቸውን? ጌታ የመለሰላቸው በሁለት መንገድ ነው:: አንደኛ በሩ ጠባብ ስለሆነ ተጋድሎ የሚጠይቅ ነው:: ምን ዓይነት ተጋድሎ ብለን ብንጠይቅ መልሱ በንስሐ ራስን መመርመርና በእግዚአብሔር ጸጋ ላይ መደገፍ ነው:: ሆኖም ግን ብዙዎች ወደዚያ የመዳን ሥፍራ ለመግባት ፈልገው እንደማይሳካላቸው ይነግረናል:: የቃል ኪዳን ልጆች ሆነው ከጸጋው ብርሃን ተቁዋዳሾች የሆኑ ማለትም ቃሉን የሰበኩ የዘመሩ በውጭ ሲጣሉ በአንጻሩ ደግሞ አመዛኙን የእድሜ ዘምናቸውን በኃጢአትና በዝሙት ያሳለፉ አመንዝራዎችና ቀራጮች እነዚያን የሃይማኖት ሰዎች ቀድመው በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ ይገኛሉ:: እድሜ ልካቸውን ስመ እግዚአብሔርን ሲጠሩ የነበሩትን አላውቃችሁም እናንት አመጸኞች ከኔ ወግዱ ሲላቸው እነዚያን ደካሞች የሥነ ምግባር ምስኪኖችን ግን እናንት ቡሩካን ይላቸዋል:: ልዩነቱ ምንድነው ብንል ንስሐ ነው:: ፊተኞች ኋለኞች የሆኑት የተከፈተላቸውን የጸጋና የምህረት በር በሃይማኖተኝነት ትምክሀት በሥሥትና በትዕቢት ስለዘጉት ነው:: ዓይናቸው በሌሎች ሰዎች ኃጢአት ላይ ስለሆነ የራሳቸውን ኃጢአት ለማየት አልቻሉም::

ይህ የጌታ ማስጠንቀቂያ ምን ያሳስበናል? መለስ ብላችሁ እንደገና ጥቅሱን አንብቡት:: ጥያቄው የሚድኑት ጥቂቶች ናቸው ወይ? ነው:: ጥቂት ያደረገው የብዙዎች በቀላሉ መንገድ መሄድ ነው:: ማስመሰል ቀላል ነው:: የባህርይ ለውጥ ከባድ ነው:: የባህርይን ለውጥ ለማምጣት ደግሞ ከባድ ስልሆነብን የመንፈስ ቅዱስ እርዳታ ሊሰጠን ቃል ተገብቶልናል:: በመሆኑም በተከፈተውና ለእኛ በተሰጠን የጸጋና የምህረት ደጃፍ እንለፍ:: በጠባቡ መንገድ እንጋደል::

የእግዚአብሔርን መንግሥት በምን እመስላታለሁ? ሉቃ 13:18-21

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የአገልግሎቱ መነሻ ያደረገው መንግሥተ ሰማያት መቅረብዋንና በንስሐ ወደዚህች የእግዚአብሔር መንግሥት መግባት እንዳለብን በማወጅ ነው:: ይህች የእግዚአብሔር መንግሥት ያላትን ባህርይ ለማስረዳት ጌታ ኢየሱስ ሁለት ምሳሌዎችን ያቀርብልናል:: አንደኛዋ የሰናፍጭ ቅንጣት ናት:: ያች ታናሽ ዘር አድጋና ቅርንጫፎቹዋን ዘርግታ ለብዙዎች አዕዋፋት ማረፊያ እንደምትሆን እንዲሁ የእግዚአብሔር መንግሥትም የብዙዎች ሕይወት እረፍት ማግኝያ እንደምትሆን ነው:: ይህም ሊታወቅ በጌታ በትምህርቱ በፈውሱና በተአምራቱ ብዙዎች በሥቃይ የነበሩ አርፈዋል:: የነፍስ እረፍትን በትምህርቱ የሥጋ እረፍትንም በተአምራቱና በፈውሱ አግኝተዋል:: ሁለተኛው ምሳሌ የእርሾው ምሳሌ በዱቄት ውስጥ የተሽሽገ እርሾ ሊጡን በሙሉ እንደሚለውጥ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መግባትም የምድራዊ ድርጅት ጉዳይ ሳይሆን ከፍተኛ የሆነ የባህርይ ለውጥ የሚያመጣ ነው:: ምን ዓይነት ባህርይ ብሎ የሚጠይቅ ሰው ቢኖር በዚሁ በሉቃስ የሜዳው ስብከት የተባለውንና በማቴዎስ የተራራው ስብከት ተብሎ የሚታወቀውን ማየት ነው:: ጌታ በተራራው ስብከት ሊያሳይ የፈለገው የእግዚአብሔር መንግሥት ዜጎች የሆኑ ሰዎች የሚኖራቸው የህይወት ለውጥን ነው:: በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ ሆነን አፍአዊ ክርስቲያን መሆን አንችልም:: በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ ሆነን በዓለማዊ አስተሳሰብ ውስጥ አንዳክርም:: እርሾው ማለትም ያ ሰማያዊ አሳብ ሙሉ በሙሉ ይለውጠናል::